ቀጥታ፡

የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ዝርያን ለማሻሻል የተጀመሩ ውጤታማ ተግባራት ይጠናከራሉ

አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ዝርያን ለማሻሻል የተጀመሩ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዳኛቸው በየነ (ዶ/ር) ገለጹ።

ባለፉት የለውጥ ዓመታት በግብርናው ዘርፍ ያሉ እምቅ ሀብቶችን ጥቅም ላይ ለማዋል የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ሲሆን የእንስሳት ምርታማነትን ለማሳደግ የተሠሩ ስራዎችም ተጠቃሽ ናቸው፡፡ 

በተለይም የሌማት ትሩፋት ተግባራዊ ከሆነ ወዲህ የእንስሳት ምርታማነት በተጨባጭ ያደገ ሲሆን የበርካቶችን ህይወት በመለወጥም ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጠ  እንደሚገኝ ነው የተመላከተው፡፡

የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዳኛቸው በየነ (ዶ/ር)፤  ኢንስቲትዩት የዳልጋ ከብቶችን ጨምሮ የእንስሳት ሃብቶች ላይ የዝርያ ማሻሻያዎችን በመሥራት የእንስሳት ተዋጽኦ አቅርቦት እንዲጨምር ትልቅ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ብለዋል፡፡ 


 

በተለይም ከፍተኛ ምርት መስጠት የሚችሉ የውጭ ዝርያዎችን በሀገር ውስጥ ካሉ ላሞችና ጊደሮች ጋር በማዳቀል የተሻሻሉ ዝርያ ያላቸው እንዲበራከቱ እያደረገ ይገኛል ብለዋል፡፡  

ይህም አርብቶና አርሶ አደሩ የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎችን እንዲያገኙ በማድረግ ከእንስሳቱ የሚያገኙት ተዋጽኦ በመጠንና በጥራት እያደገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ለዚህም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተግባራዊ የተደረገው የሌማት ትሩፋት ዘርፉ ከፍተኛ ትኩረት እንዲያገኝ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡


 

በቀጣይም በሰው ሰራሽ ዘዴ የማዳቀል፣ የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን የመጠቅምና ባለሙያዎች ተጨማሪ ክህሎት እንዲያገኙ የማድረግ ሥራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል፡፡

ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አያይዘውም፤ ኢንስቲትዩቱ የሚያመርተውን የፈሳሽ ናይትሮጂን ደህንነቱ ተጠብቆ ለእንስሳት ዝርያ ማሻሻያ ተግባር እንዲውል እየተደረገ መሆኑንም አክለዋል። 

ኢንስቲትዩቱ በበጀት ዓመቱ 4 ነጥብ 9 ሚሊዮን ላሞችና ጊደሮችን ለማዳቀል የተያዘውን ግብ ለማሳካት እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

የሆለታ እንስሳት ልማት ማዕከል ኃላፊ አራርሳ ዱጉማ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ማዕከሉ ኢትዮጵያ በእንስሳት ዘርፉ ላይ ያላትን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎችን እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡


 

በዚህም ዝርያዎችን የማሻሻል፣ የእንስሳት አዳቃይ ቴክኒሺያኖችን የማሰልጠንና የተቀነባበረ መኖ ማምረትን ጨምሮ ሌሎችንም ስራዎች እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

ማዕከሉ የተሻሻሉ ጊደሮችን ለተጠቃሚዎች ተደራሽ በማድረግ ላይ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም