ቀጥታ፡

በካፋ ዞን 860 ሄክታር መሬት በበጋ  መስኖ የስንዴ ልማት በዘር ተሸፍኗል 

ቦንጋ ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡-በካፋ ዞን በበጋ መስኖ የስንዴ ልማት ከ860 ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና፤ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ ልማት መምሪያ አስታወቀ።

በተደረገላቸው ድጋፍ በማህበር ተደራጅተው 10 ሄክታር መሬት ላይ ካለሙት የስንዴ ሰብል የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ የገለጹት ደግሞ በሺሾ እንዴ ወረዳ የዋናቦላ ወጣቶች ናቸው።

የበጋ መስኖ የስንዴ ልማት ስራ የአርሶ አደሩን የስራ ባህል ከመቀየርና ከውጭ የሚገባውን ምርት በሃገር ውስጥ ከመተካት ባለፈ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥና የስራ ዕድል ከመፍጠር አንጻር ቅልቅ ውጤት እየተመዘገበበት ይገኛል።


 

በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ካፋ ዞን በ2018 በጀት ዓመት ከ2 ሺህ 422 ሄክታር በላይ መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ በማልማት ወደ 84 ሺህ 796 ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል።

በዞኑ ግብርና አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ ልማት መምሪያ የእርሻ ዘርፍ ሀላፊ አቶ አክሊሉ አማዴ ለኢዜአ እንዳሉት፤ እስከአሁን 1 ሺህ 222 ሄክታሩ መሬት የታረሰ ሲሆን ከዚህ ውስጥ ከ860 ሄክታር የሚበልጠው በዘር ተሸፍኗል።


 

ለዚህ የሚሆን ከ900 ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር እና በቂ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱንም ጠቁመዋል።

አርሶ አደሩ የደረሱ የመኸር ሰብሎችን ፈጥኖ በመሰብሰብ የመስኖ አውታሮችንና በአካባቢው የሚገኙ የተለያዩ የውሃ አማራጮችን ተጠቅሞ ወደ በጋ መስኖ ስንዴ ልማት እንዲገባ እየተሰራ ነው ብለዋል።

የሺሾእንዴ ወረዳ ግብርና አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ ልማት ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አዱኛ አለሙ፤ በወረዳው ዘመናዊ የመስኖ ተቋምና የተለያዩ የውሃ አማራጮችን በመጠቀም 316 ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ እየለማ መሆኑን ገልፀዋል። 


 

በወረዳው ዋና ቦላ ቀበሌ የተገነባው ጋሻ ገጨራ የመስኖ አውታር ከ98 ሄክታር በላይ ማሳ የማልማት አቅም ያለው ሲሆን ከዚህ ውስጥ ወጣቶችን በማደራጀትና የግብዓት ድጋፍ በማድረግ የለማው 10 ሄክታር የስንዴ ማሳ የተሻለ ተሞክሮ የሚቀመርበት ነው ብለዋል።

በወረዳው በዋናቦላ ቀበሌ ሰባት ወጣቶች ሆነው በማህበር በመደራጀት የተሰጣቸውን 10 ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ማልማት እንደቻሉ የማህበሩ ፀሐፊ ወጣት ብርሃኑ ገብረጊዮርጊስ ገልጿል።


 

ወረዳው ባደረገላቸው ድጋፍም ማሳቸውን በትራክተር በማሳረስ 10 ሄክታር መሬት ላይ ስንዴ አልምተው ቡቃያው በጥሩ ቁመና ለይ እንደሚገኝና በሄክታር እስከ 40 ኩንታል ምርት እንደሚጠብቁ ተናግሯል።


 

የማህበሩ አባል የሆነው ወጣት እሚቶ መጫሎ ፤ በበጋ ወቅት እርሻ ብዙም ያልተለመደ መሆኑን ገልጾ በአካባቢው የተገነባው የመስኖ አውታር አዲስ የስራ ባህል መፍጠሩን ተናግሯል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም