ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የዲጂታል ፋይናንስና የክፍያ ሥርዓት በፈጣን የዕድገት ጎዳና ላይ ነው- የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ(ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30፣ 2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የዲጂታል ፋይናንስና የክፍያ ሥርዓት በፈጣን የዕድገት ጎዳና ላይ መሆኑን የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ።

ከ2026 - 2030 የሚተገበረው ብሔራዊ የዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ ዛሬ በሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህና ሌሎችም የመንግሥት ከፍተኛ አመራር አባላት በተገኙበት ይፋ ተደርጓል።


 

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ( ዶ/ር) በኢትዮጵያ የዲጂታል ለውጥ ከፍተኛ እድገት ላይ እንደሚገኝ በአፅንኦት ገልጸዋል።

የዲጂታል ክፍያ ሥርዓቶች ከፍተኛ ተቀባይነት እያገኙ እና ለኢኮኖሚ እድገት ጉልህ ሚና እያበረከቱ መሆኑንም ጠቅሰዋል።

ኢትዮጵያ አስደናቂ የሆነ የዲጂታል ለውጥ እያስተናገደች መሆኗን ገልጸው፤ ይህም ለፋይናንስ ዘርፉ ዕድገት ትልቅ መስፈንጠሪያ እየሆነ መምጣቱን አንስተዋል።

በሀገር አቀፍ ደረጃ ፈጠራን የሚያበረታቱ አሠራሮችና በዲጂታል መሠረተ ልማት ላይ እየተደረጉ ያሉ ኢንቨስትመንቶችም ለዕድገቱ ሚናቸው የላቀ ነው ብለዋል።

በኢትዮጵያ የዲጂታል ግብይቶች ፈጣን ዕድገት እያሳዩ ነው ያሉት የባንኩ ገዥ፤ ይህም በሀገሪቷ የግብይት ገጽታ ላይ ታሪካዊ ለውጥ ማምጣቱን ጠቁመዋል።

ይህ የዲጂታል ግብይት መጨመር፣ የዲጂታል ክፍያዎች ተቀባይነት እየጨመረ መምጣቱን የሚያሳይ መሆኑንም ተናግረዋል።

በብሔራዊ የክፍያ መሠረተ ልማቶች ላይ እየተደረጉ ያሉ የማሻሻያ ሥራዎች ቅልጥፍናንና ደህንነትን እያሻሻሉ ሲሆን፤ ጠንካራ የዲጂታል ፋይናንስ ሥርዓት እንዲኖር መሠረት እየጣሉ ነው ብለዋል።

ሰፊ የዲጂታል እምቅ አቅም ያላት ኢትዮጵያ በፍጥነት እያደገ ያለ የፋይናንስና የግብይት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን ገልጸዋል።

እነዚህ ስኬቶች ቢኖሩም በቴክኖሎጂ ተደራሽነት ያሉ ክፍተቶች፣ የአጣዳፊ ጊዜ አገልግሎቶች አለመስፋት እና እያደጉ የመጡ የሳይበር ደህንነት ስጋቶችን ጨምሮ ፈተናዎች መኖራቸውን ጠቅሰዋል።

እነዚህን ፈተናዎች ለመፍታት በመንግሥት እና የግል ዘርፉ ትብብር አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።

የብሔራዊ ዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ (2026-2030) በፋይናንስ አገልግሎት ውስጥ አካታችነትን እንደሚያጎለብት እና ፈጠራን እንደሚያበረታታም ነው የገለጹት ገዥው።

አዲሱ ስትራቴጂ አስተማማኝ እና ተዓማኒ የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት መዘርጋት፣ የፋይናንስ አገልግሎቶች ዲዛይን ውስጥ የፆታ አቀፍ ተጠቃሚነትን ማሳደግ እና ከድንበር ተሻጋሪ ክፍያዎች ጋር የሚጣጣም የክፍያ ስርዓትን መፍጠርን ያካትታል ብለዋል።

በተጨማሪም ስትራቴጂው የብሔራዊ መረጃ ልውውጥ እንዲቋቋም እና የአስፈላጊ አገልግሎቶችን ተደራሽነት ለማስፋት ድጋፍ እንደሚያደርግ አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም