ሀገር አቀፍ የፖሊዮ መከላከያ ክትባት ዘመቻ ይካሄዳል-ኢንስቲትዩቱ - ኢዜአ አማርኛ
ሀገር አቀፍ የፖሊዮ መከላከያ ክትባት ዘመቻ ይካሄዳል-ኢንስቲትዩቱ
አዳማ፤ ሕዳር 29/2018(ኢዜአ )፡- ሀገር አቀፍ የፖሊዮ መከላከያ ክትባት ዘመቻ ከታህሳስ 3 እስከ 6/2018 ዓ.ም የሚካሄድ መሆኑን የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታወቀ።
የክትባት ዘመቻውን ለማሳካት ያለመ የባለድርሻ አካላት የንቅናቄ መድረክ ዛሬ በአዳማ ከተማ ተካሂዷል።
በኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የበሽታዎች ቅኝትና ቅድመ ማስጠንቀቂያ ዳይሬክተር አቶ እንዳለ ዘመነ እንደገለጹት፤ ፖሊዮን ለማጥፋት የተቀናጀ ሀገር አቀፍ ክትባት ዘመቻ በመላው ሀገሪቱ ይካሄዳል።
ዘመቻውን ስኬታማ ለማድረግ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ግንዛቤ ከመፍጠር ጀምሮ ድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።
የክትባት ዘመቻው 25 ሚሊዮን የሚሆኑ ሕፃናት ተደራሽ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል።
በዚህም በሁሉም ክልሎች የክትባቱ ቁሳቁስና ተያያዥ ግብዓት አቅርቦት በየወረዳዎቹ የጤና ተቋማት ደርሰው ወደ ቀበሌዎች እየተሰራጩ እንደሚገኙ አንስተው፤ የሰው ሃይል ዝግጅትን ጨምሮ የሕብረተሰብ ንቅናቄ መካሄዱንም አክለዋል።
በዘመቻው የቤት ለቤት የፖሊዮ ክትባት ከመስጠት ጎን ለጎን የበሽታው ምልክት ያሳዩትን ሕፃናት የመለየት ስራ እንደሚከናወን አስረድተዋል።
በጤና ሚኒስቴር የክትባት ፕሮግራም የኮሙኒኬሽን አማካሪ ወይዘሮ ፀጋነሽ ገድሉ እንዳመለከቱት፤ በዘመቻው መደበኛ የፖሊዮ ክትባት ያልወሰዱ ሕፃናት ይካተቱበታል።
በጊዜያዊ የክትባት ጣቢያዎችና ወደ ጤና ተቋማት ሄደው ክትባቱን እንዲወስዱ የማድረግ ስራ ይሰራል ነው ያሉት ።
ክትባቱ በሁሉም ክልሎች በሚገኙ ከተሞች፤ ወረዳዎችና ቀበሌዎች በተመሳሳይ ወቅት እንደሚሰጥ ጠቁመው፤ ለስኬታማነቱም በየደረጃው የሚገኙ ባለድርሻ አካላት ትብብርና ዕገዛ እንዲያደርጉ መልዕክት አስተላልፈዋል ።