የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ልማት ለሰላማዊ አገልግሎት ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል ነው - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ልማት ለሰላማዊ አገልግሎት ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል ነው
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 29/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ልማት መርሃ ግብር ለሰላማዊ አገልግሎት ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል መሆኑን የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኢነርጂ ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ ገለጹ።
የኢትዮጵያን የኒውክሌር ኃይል ልማት መርሃ ግብር ማስጀመሪያና የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ኮሚሽን ሥራ ማስጀመሪያ የምክክር መድረክ በመካሄድ ላይ ይገኛል።
በመድረክ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኢነርጂ ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ፣ የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሚካኤል ቹዳኮቭና የባለድርሻ ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኢነርጂ ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ ፤ የኢትዮጵያ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ልማት የኃይል ደህንነትን በማረጋገጥ የኢኮኖሚያዊ ሽግግርና የረጅም ጊዜ የመቋቋም አቅም ግንባታ ላይ የተመሠረተ ብሔራዊ የልማት ተነሳሽነት ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ንጹህ የኃይል አቅርቦት የማመንጨት አቅምን በማላቅ በጤና፣ ግብርና፤ በኢንዱስትሪ እና የምርምር ትግበራ ማዕቀፍ የተቃኘ መሆኑን ገልጸዋል።
የሰላማዊ አማራጭ የኒውክሌር ሳይንስ ልማት መርሃ ግብሩ ዓላማ የኢትዮጵያዊያንን ህይወት በተጨባጭ የሚያሻሽሉ ጥቅሞችን የሚያስገኝ ዕድል ማረጋገጥ እንደሆነም ተናግረዋል።
የኃይል አቅርቦት የዕድገት ሞተር ነው ያሉት ኮሚሽነሩ የሰላማዊ አማራጭ አስተማማኝ የኒውክሌር ኃይል ልማት መርሃ ግብር የኢትዮጵያን ዕድገት ጥራትና ፍጥነት ይቀርፃል ብለዋል።
የኢትዮጵያ መንግሥት የኒውክሌር ኃይል ልማት ቁርጠኝነት ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገትን ማረጋገጥ ታሳቢ ያደረገ ደፋር ውሳኔ መሆኑን አብራርተዋል።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ምረቃ ላይ በጉባ ከተበሰሩ ማግስት በሩሲያ የተካሄደው ዓለም አቀፍ የአቶሚክ ኃይል መድረክ ድረስ ኢትዮጵያ ለሰላማዊ የኒውክሌር ልማት ያላትን ቁርጠኝነት ማረጋገጣቸውን አስታውሰዋል።
በዚህም ኢትዮጵያ የኒውክሌር ቴክኖሎጂን ለሰላማዊ አገልግሎት ብቻ ለመጠቀም ሙሉ በሙሉ ቁርጠኛ ነች ብለዋል።
የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ኮሚሽን በተሰጠው ግልጽ ሥልጣንና ጠንካራ መዋቅር ከዓለም አቀፍ የአቶሚክ ኢነርጂ ጋር በቁርጠኝነት እንደሚሰራ ገልጸዋል።
የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ጋር የተፈጠረው የሥልጠና ፕሮግራምና የባለሙያ የልምድ ልውውጥ፣ ክህሎት ግንባታና የቴክኒክ ትብብር እየተሳለጠ መሆኑን ተናግረዋል።
በቀጣይም ኢትዮጵያ በዕውቀትና በሰላማዊ የኒውክሌር ልማት የጋራ ርዕይ በመመስረት ከዓለም አቀፍ አቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ጋር የትብብር ስራን አጠናክራ እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል።