ኢንዱስትሪዎች የሚፈልጉትን ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት የተሰጠው ትኩረት ውጤት እያመጣ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ኢንዱስትሪዎች የሚፈልጉትን ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት የተሰጠው ትኩረት ውጤት እያመጣ ነው
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 28/2018 (ኢዜአ)፦የአካባቢን ፀጋ መሰረት ባደረገ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንዱስትሪዎች የሚፈልጉትን ብቁ የሰው ኃይል የማፍራት ሥራ ውጤት እያመጣ መሆኑን የተለያዩ የክልል የቢሮ ኃላፊዎች ገለጹ።
ኃላፊዎቹ እንዳሉት፡ በቴክኒክና ሙያ ስልጠና ተቋማትና ኢንዱስትሪዎች ትስስር በመፍጠር ሠልጣኞች የተግባር ትምህርት በአግባቡ እንዲያገኙና በፍጥነት ወደ ሥራው ዓለም እንዲቀላቀሉ እያስቻለ ነው።
የድሬዳዋ አስተዳደር ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ሮቤል ጌታቸው፤ የቴክኒክና ሙያ ስልጠናው ገበያን መሰረት አድርጎ መስጠት መጀመሩ ሠልጣኞች በሥራ ገበያው ያላቸውን ተወዳዳሪነት ማሳደጉን ገልጸዋል።
ለሥራ ዕድል ፈጠራ ትልቅ ሚና እንዳለው በማንሳትም፥ ባለፈው ዓመት ብቻ ለ19 ሺህ ዜጎች በዚህ ዓመት ደግሞ እስካሁን ለ4 ሺህ 700 ዜጎች የሥራ እድል መፍጠር መቻሉን ነው የገለጹት።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ሙስጠፋ ኢሳ በበኩላቸው፤ በቴክኒክና ሙያ እየተሰጠ ያለው የአጫጭር እና መደበኛ ስልጠና የሥራ ፈጣሪነት አቅምን እያጎለበተ ነው ብለዋል።
ጥራት ያለው ስልጠና በመስጠት ገበያው የሚፈልገውን የሰው ኃይል በማፍራት ረገድ ውጤት ማምጣት መቻሉን አመልክተዋል።
የቴክኒክና ሙያ ዘርፉን አቅም ይበልጥ ለማሳደግ የተሻለ ጥራት ያለው ስልጠና የመስጠት ሰፋፊ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው ያሉት ደግሞ የኦሮሚያ ክልል ሥራ እድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ኤባ ገርባ ናቸው።
በዚህም በከተማም ሆነ በገጠር እየተፈጠሩ ያሉ የልማት አቅሞች ለቴክኒክና ሙያ ሰልጣኞች ሰፊ የሥራ እድል እየፈጠሩ መሆኑን ጠቅሰዋል።
የአማራ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አማረ አለሙ፤ የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ሪፎርም ኮሌጆች ተልእኳቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ከማድረግ ባለፈ በቂ ክህሎት የተላበሰ ዜጋ ለማፍራት እያስቻለ ነው ብለዋል።
ስልጠናዎች በየአካባቢው ያለው የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የሚፈልገውን የሰው ኃይል መሰረት አድርገው እንዲሰጡ መደረጉ ውጤት እያመጣ መሆኑን አብራርተዋል።
የአፋር ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አህመድ ኢብራሂም፤ የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች በየአካባቢው ያለውን ፀጋ መሰረት አድርገው ስልጠና መስጠታቸው በሥራ ዕድል ፈጠራና በኢኮኖሚ ለውጥ እንዲመጣ አስችለዋል ነው ያሉት።
የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ዜጎች በሥራና በፈጠራ ውጤት ሃብት መፍጠር እንዲችሉ እያደረገ ነው ያሉት ደግሞ የሲዳማ ክልል ስራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ሀገረጽዮን አበበ ናቸው ።
በክልሉ ሰልጣኞች ከኢንዱስትሪዎች ጋር ትስስር እንዲፈጥሩ ከማድረግ አንፃር ስኬታማ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝም ነው የተናገሩት።