የመደመር መንግሥት የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የመደመር መንግሥት የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ ነው
አዲስ አበባ፤ ህዳር 27/2018(ኢዜአ)፦ የመደመር መንግሥት የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑ ተገለጸ።
"የጉባ ብስራቶች፣ የመደመር መንግሥት ቱሩፋቶች" በሚል መሪ ሀሳብ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ በአዲስ ዓለም-አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል የአዲስ አበባ ነዋሪዎች የውይይት መድረክ ተካሂዷል።
የውይይት መድረኩ በመደመር እሳቤ ሀገርን ወደ ተምሳሌት ለመቀየር የተሰራበት ሂደት፣ አርቆ በማሰብ የመፈፀም ብቃት የታየበት ሁኔታ፣ በመስራት የሀገር የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት እንዲረጋገጥ የተሰራበት ሂደትና ሌሎች ጉዳዮች ተመክሮባቸዋል።
በተለይም በትምህርት፣ በጤና፣ በከተማ ግብርና፣ በስራ እድል ፈጠራ፤ በሰው ተኮር ተግባር፣ በሌማት ቱሩፋት፣ በበጎ ፍቃድ ተግባራት፣ በትራንስፓርት አገልግሎትና በመልካም አስተዳደር የተሰሩ ስራዎችና ቀጣይ ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች ውይይት ተደርጎባቸዋል።
ከተሳታፊዎችም የተለያዩ አስተያየትና ጥያቄዎች ተነስተው ውይይት ተደርጎባቸዋል፣ ከመድረኩ መሪዎችም ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል።
የመልካም አስተዳደርና አገልጋይነት ጥያቄ፣ የመሬት አስተዳደርና የአርሶ አደሮች ተጠቃሚነት፣ እንዲሁም ሌሎች ቢስተካከሉ የተባሉ ጉዳዮች በተሳታፊዎች ተነስተዋል።
የህዝብን ጥያቄዎች በትኩረት በማዳመጥ ምላሽ መስጠት እንደ መንግስት አቅጣጫ ተይዞ እየተሰራ ነው፣ ይህ ውይይት መድረክም የዚሁ አካል መሆኑን በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊና የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አለምፀሀይ ሽፈራው አስገንዝበዋል።
ለጋራ ሀገራዊ ልማትና ብልፅግና ስንረባረብ ምን ማሳካት እንደሚቻል አዲስ አበባ አብነት መሆኗንም ጠቁመዋል
የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙም ገልፀዋል።
ከመልካም አስተዳደርና ብልሹ አሰራር ጋር የተያያዙ ችግሮችን ከመሰረቱ ለመፍታት ለአንድ ማዕከል አገልግሎት ትኩረት መሰጠቱንም አብራርተዋል።
የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ አስተባባሪ ሚኒስትር መለስ ዓለሙ በበኩላቸው ከኑሮ ውድነት ጋር የተያያዙ ችግሮችን ለመቅረፍ ሰው ተኮር ልማቶችና አምራችነት ላይ በትኩረት መሰራቱን ገልፀዋል።
ከመድረኩ የተገኙ ግብዓቶችን የቀጣይ ልማትና መልካም አስተዳደር እቅዶች አካል በማድረግ ሁለንተናዊ ውጤት ለማስመዝገብ እንደሚተጉ የገለፁት ደግሞ የባህልና ስፖርት ሚኒስትሯ ሻዊት ሻንካ ናቸው።
በህዝባዊ የውይይት መድረኩ ከሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የተወጣጡ ነዋሪዎች የተሳተፉ ሲሆን የለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈፃሚን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛና መካከለኛ የስራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል።