ኢትዮጵያ ስሟንና ታሪኳን የሚመጥኑ በርካታ ትልልቅ ፕሮጀክቶችን ጀምራ መጨረስ የምትችል ሀገር ሆናለች - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ ስሟንና ታሪኳን የሚመጥኑ በርካታ ትልልቅ ፕሮጀክቶችን ጀምራ መጨረስ የምትችል ሀገር ሆናለች
አዲስ አበባ፤ ህዳር 27/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ስሟንና ታሪኳን የሚመጥኑ በርካታ ትልልቅ ፕሮጀክቶችን ጀምራ መጨረስ የምትችል ሀገር መሆኗን በአዲስ አበባ ከተማ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ በተካሄደው ህዝባዊ መድረክ የተሳተፉ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ።
በዛሬው እለት በአዲስ አበባ የተለያዩ ክፍለ ከተሞች የተካሄደው ህዝባዊ ውይይት በቂርቆስ ክፍለ-ከተማም ተከናውኗል።
በውይይት መድረኩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ(ዶ/ር) እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
"የጉባ ብስራቶች፣ የመደመር መንግስት ትሩፋቶች" በሚል መሪ ሀሳብ በተካሄደው ህዝባዊ ውይይቱ ላይ ነዋሪዎቹ በኢትዮጵያ በርካታ የልማት ውጤቶች ተመዝግበዋል ሲሉ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ስሟንና ታሪኳን የሚመጥኑ በርካታ ትልልቅ ፕሮጀክቶችን ጀምራ መጨረስ የምትችል ሀገር ሆናለች ያሉት ተወያዮቹ ለዚህም በመንግስት በኩል የተሰጠው ትኩረትና የአመራር ቁርጠኝነት ውጤት ስለሆነ ሊመሰገን ይገባዋል ብለዋል።
እንደሀገር የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎች ሊደገፉ የሚገባቸው መሆኑን ጠቁመው፤ የመኖሪያ ቤት ግንባታን ማጠናከር፣ የሥራ ዕድል ፈጠራን ማስፋፋት እና የኑሮ ውድነትን ማረጋጋት ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸውም ጠቁመዋል፡፡
ውይይቱን የመሩት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ(ዶ/ር) በውይይቱ የተነሱ ጉዳዮች ላይ መንግስት በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል።
መንግስት አስቀድሞ በሁሉም አካባቢዎች የጀመራቸውና የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ ስራዎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።
አመራሮቹ የመደመር መንግሥት ግብ በሀገራቸው የሚኮሩ ቅን ኢትዮጵያውያንን መፍጠር መሆኑን ገልጸው፤ የዜጎችን ቀጥተኛ ተጠቃሚነትና የኑሮ ደረጃ ማሻሻል ላይ ያተኮሩ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል፡፡
ህብረ ብሔራዊት ኢትዮጵያ በመደመር ወደ ሁለንተናዊ ብልፅግና የምታደርገው ጉዞ አጠናክራ መቀጠል አለባት ሲሉም ተሳታፊዎቹ ገልፀዋል፡፡