ማዕከሉ ድርቅንና በሽታን በመቋቋም በእጥፍ ምርት የሚሰጡ የተሻሻሉ የማሽላ ዝርያዎችን እያላመደ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ማዕከሉ ድርቅንና በሽታን በመቋቋም በእጥፍ ምርት የሚሰጡ የተሻሻሉ የማሽላ ዝርያዎችን እያላመደ ነው
ጂንካ፤ ህዳር 27/2018(ኢዜአ)፦ የጂንካ ግብርና ምርምር ማዕከል ድርቅንና በሽታን በመቋቋም በእጥፍ ምርት መስጠት የሚችሉ ከ374 በላይ የተሻሻሉ የማሽላ ዝርያዎችን እያላመደ መሆኑን ገለጸ።
የምርምር ማዕከሉ በተሻሻሉ የማሽላ ዝርያዎች ላይ እያከናወነ ያለው የጥናትና ምርምር ስራ ዛሬ ምልከታ ተካሂዷል።
የማዕከሉ ዳይሬክተር እና የሰብል ተመራማሪ ተክሌ ዮሴፍ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት ማዕከሉ የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎችን በማላመድ የአካባቢውን አርሶ እና አርብቶ አደሮች ተጠቃሚ ለማድረግ እየሰራ ነው፡፡
በተለይም እየተላመደ ያለው ማሽላ ድርቅን የመቋቋም አቅሙ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመው የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ተመራጭ የሰብል አይነት መሆኑን ጠቁመዋል።
የማሽላ ዝርያው ከምግብ ፍጆታነት ባለፈ ተረፈ ምርቱ ለከብቶች መኖነትና ለቤት መስሪያነት የሚያገለግል በመሆኑ ዝናብ አጠር በሆኑ ቆላማ አካባቢዎች ተመራጭ ነው ብለዋል፡፡
የሰብል ተመራማሪው አወቀ ታደሰ በበኩላቸው የምርምር ማዕከሉ ከ374 በላይ የማሽላ ዘረመሎችን ከሀገር ውስጥና ከውጭ ሀገራት በማስመጣት ላለፉት ሶስት ወራት ምርምር ሲያካሄድ መቆየቱን ተናግረዋል።
በምርምር ማዕከሉ ውጤታማነታቸው ከተረጋገጡ የማሽላ ዝርያዎች ''መልካም'' የተሰኘው የማሽላ ዝርያ ተጠቃሽ ሲሆን በሄክታር እስከ 55 ኩንታል ምርት እንደሚሰጥ ገልጸዋል፡፡
የማሽላ ዝርያዎቹ ከአካባቢው የማሽላ ዝርያዎች ጋር ሲነፃፀሩ ድርቅንና በሽታን በመቋቋም በእጥፍ ምርት መስጠት የሚችሉና በአጭር ጊዜ የሚደርሱ መሆናቸው ተመራጭ አድርጓቸዋል ብለዋል።
በምስክ ምልከታው የተገኙት የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አብረሃም አታ በበኩላቸው የምርምር ማዕከሉ ችግር ፈቺ የጥናትና ምርምር ስራዎችን በማከናወን የአካባቢውን አርሶ አደሮች ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በምርምር ማዕከሉ የተመለከቷቸው የጥናትና ምርምር ስራዎች መንግስት ግብርናውን በማዘመን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እያደረገ ላለው ጥረት አጋዥ ናቸው ብለዋል፡፡
የምርምር ማዕከሉ በዞኑ ለሚከናወኑ የግብርና ልማት ስራዎች የምርምር ውጤቶችን በማበርከት ትልቅ እገዛ እያደረገ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የአሪ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ ጉራልቅ ይዥማልቅ ናቸው።
አካባቢው ለማሽላ ምርት ተስማሚ ስነ-ምህዳር ያለው በመሆኑ በምርምር ማዕከሉ ውጤታማነታቸው የተረጋገጡ የማሽላ ዝርያዎችን ወደ አርሶ አደሩ የማስፋት ስራ እንደሚከናወንም ገልጸዋል፡፡
በመስክ ምልከታው ላይም የዞኑ ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ስመኝ ተስፋዬን ጨምሮ ሌሎች አመራሮች ተገኝተዋል።