ቀጥታ፡

በኢትዮጵያ በቴክኖሎጂና ዲጂታላይዜሽን ዘርፍ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር በአርዓያነት የሚወሰድ አስደናቂ ሥራ እየተሰራ ነው

አዲስ አበባ፤ ህዳር 27/2018(ኢዜአ):- በኢትዮጵያ በቴክኖሎጂና ዲጂታላይዜሽን ዘርፍ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር በአርዓያነት የሚወሰድ አስደናቂ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ለፓን አፍሪካ ንቅናቄና ለአፍሪካ ሕብረት ምስረታ ጉልህ አበርክቶ የነበራቸው የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች ልጆችና የልጅ ልጆች ገለጹ።

ለፓን አፍሪካ ንቅናቄና ለአፍሪካ ሕብረት ምስረታ ጉልህ አበርክቶ የነበራቸው የአፍሪካ መሪዎች ልጆችና የልጅ ልጆች የሳይንስ ሙዝየም ቋሚ ኤግዚቢሽንን ትላንት ማምሻውን ጎብኝተዋል።

በጉብኝቱ ላይ የመጀመሪያው የዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት የፓትሪስ ሉሙምባ ልጅ፣ የመጀመሪያው የጋና ፕሬዝዳንት ኩዋሜ ኑኩሩሃማ ልጅ፣ የኩዋሜ ኑኩሩማ የልጅ ልጅ፣ የመጀመሪያው የዛምቢያ ፕሬዝዳንት ኬኔት ካውንዳ ልጅ፣ የቀድሞ የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ኔልሰን ማንዴላ የልጅ ልጅ እና የታንዛኒያ የመጀመሪያ ፕሬዝዳንት ጁሊየስ ኔሬሬ ልጅ ተሳትፈዋል።

በተጨማሪም ታዋቂው ደቡብ አፍሪካዊ ፀረ አፓርታይድ ታጋይ ስቲቭ ቢኮ ልጅ፣ የፀረ አፓርታይድ ታጋይና ሚኒስትር የነበሩት ደቡብ አፍሪካዊ ዋልተር ሲሱሉ ሴት ልጅ፣ የአፍሪካ ብሄራዊ ኮንግረስ ፕሬዝዳንት፣ የፀረ አፓርታይድ ፖለቲከኛና አክቲቪስት ኦሊቨር ታምቦ ሴት ልጅና ሌሎችም ተገኝተዋል።

የቀድሞው የጋና ፕሬዚዳንት ክዋሜ ንክሩማ የልጅ ልጅ ክዋሜ ቶማስ፤ የአፍሪካ ሀገራት መንግስታት የቴክኖሎጂ ለአህጉሪቷ ዜጎች ቅንጦት ሳይሆን ወሳኝነቱን ታሳቢ ያደረገ ስራ መስራት ይኖርባቸዋል ብሏል።

ኢትዮጵያ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ ግብርና፣ ታዳሽ ኃይል አስደናቂ ስራ እየሰራች መሆኗን በሳይንስ ሙዝየም ቋሚ ኤግዚቢሽን መመልከቱንም ገልጿል።

የቀድሞው የጋና ፕሬዚዳንት ክዋሜ ንክሩማ ልጅ ሳሚያ ያባ ክርስቲና፤ በአፍሪካ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ልማትን የሚያሳልጡ በዕውቀትና ክህሎት የበለጸገ የሰው ሃይል ማፍራት እንደሚያስፈልግ ገልጻለች።


 

በኢትዮጵያም በሳይንስና ቴክኖሎጂ ልማት እየተከናወነ የሚገኘው አስደናቂ ስራ የአህጉራዊ የቴክኖሎጂ መሪ ተዋናይነቷን እንደሚያሳድግ ተናግራለች።

የጸረ-አፓርታይድ ፖለቲከኛ፣ አክቲቪስትና የአፍሪካ ብሔራዊ ኮንግረስ ፕሬዚዳንት የነበሩት ኦሊቨር ታምቦ ልጅ ኖማቴምባ ታምቦ፤ በፓን-አፍሪካኒዝም መንፈስ የአህጉሪቷ ወጣቶች የሚማማሩበትን መድረክ መፍጠር ያስፈልጋል ብላለች።


 

አፍሪካዊያንም የአኗኗር ባህል የእርስ በእርስ ልምድ ልውውጥ በማድረግ አሰባሳቢ ጉዳዮች ላይ በትኩረት መስራት እንዳለባቸው ገልጻለች።

የፓን አፍሪካ ንቅናቄና አፍሪካ ሕብረት መስራች ተዋንያን የአፍሪካ መሪዎች ልጆችና የልጅ ልጆች የሳይንስ ሙዝየም ቋሚ ኤግዚቢሽን የቴክኖሎጂና ዲጂታላይዜሽን የልማት ስራዎች ገለጻ ተደርጎላቸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም