የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ አገልግሎቶችን በተቀላጠፈ መልኩ ለማግኘት አስችሎናል- ነዋሪዎች - ኢዜአ አማርኛ
የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ አገልግሎቶችን በተቀላጠፈ መልኩ ለማግኘት አስችሎናል- ነዋሪዎች
ቦንጋ፤ ህዳር 26/2018 (ኢዜአ)፡-የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ባለቤት መሆን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶችን በተቀላጠፈ መልኩ ለማግኘት እንዳስቻላቸው የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በተያዘው ዓመት 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎችን የፋይዳ መታወቂያ ባለቤት ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ያስታወቀው ደግሞ የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ ነው፡፡
ብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ የዜጎችን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ዕድገት የሚያረጋግጥ፣ ሀገርንም ተወዳዳሪ የሚያደርግ ነው።
በኢትዮጵያ የነዋሪዎችን የመታወቅ መብት ለማረጋገጥ፣ በአገልግሎት ሰጭና ተቀባዮች መካከል መተማመንን ለማዳበር እንዲሁም ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው የአሰራር ስርአትን ለማስፈን ብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ተግባራዊ ተደርጓል።
መታወቂያው የአገልግሎት ሰጪና ተቀባዮችን በማስተሳሰር እንደሃገር የተያዘውን የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬታማ ለማድረግም ቁልፍ ሚና አለው፡፡
በጉዳዩ ላይ ለኢዜአ ያነጋገራቸው የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎችም የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት መሆናቸው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶችን በተቀላጠፈ መልኩ ለማግኘት እንዳስቻላቸውና ዲጂታል ኢኮኖሚን ለመቀላቀል እያገዛቸው መሆኑን ተናግረዋል።
ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ሃብታሙ ወልደስላሴ እና አቶ ተረፈ ገነሜ እንደተናገሩት ብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ) በየትኛውም ቦታ አገልግሎቶችን በቀላሉ ለማግኘት አስችሏቸዋል፡፡
መታወቂያው ከግለሰብ ባለፈ ለሀገርም ጥቅሙ የጎላ መሆኑን ጠቅሰው፣ በዲጅታል የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ውስጥ ለመሳተፍና ፈጣን አገልግሎት ለማግኘት እየጠቀማቸው መሆኑን ተናግረዋል።
በተለይ በተለያዩ ተቋማት ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎት ለማግኘት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል።
ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ ፍሬሕይወት ገዛሃኝ በበኩላቸው፣ ዲጂታል መታወቂያ ኢትዮጵያዊነትን በሚገልጽ መልኩ መዘጋጀቱ ከቦታ ቦታ በነጻነት ለመንቀሳቀስ እንዳገዛቸው ተናግረዋል።
ከዚህ ቀደም መታወቂያ ለማውጣትና ለማሳደስ እንግልት ይገጥማቸው እንደነበር አስታውሰው፣ "ዲጂታል አገልግሎቱ ይህን ችግር ከማስቀረት ባለፈ የተለያዩ አገልግሎቶችን በቀላሉ ለማግኘት አስችሎኛል" ብለዋል።
ዜጎች በሚፈለገው መጠን የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ባለቤት እንዲሆኑና ከወቅቱ ጋር ለመዘመን ቀጣይነት ያለው የግንዛቤ ሥራ መስራት እንደሚገባም አስተያየት ሰጪዎቹ ተናግረዋል።
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ምትኩ አስፋው በበኩላቸው፣ የክልሉን ህዝብ የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
ፋይዳ መታወቂያ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ አገልግሎቶችን በቀላሉ ለማግኘት የሚያስችልና እንደሀገር የተጀመረውን የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬታማ ለማድረግ ቁልፍ ሚና አለው ብለዋል፡፡
መታወቂያውን መያዝ በየትኛውም አካባቢ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶችን በተሻለ ፍጥነትና ግልጽነት ለማግኘት እንደሚያስችልም አስረድተዋል።
በክልሉ በተያዘው ዓመት 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎችን የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ሃላፊው እስካሁንም ከ223 ሺህ በላይ ሰዎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።
ዕቅዱን ለማሳካት የግንዛቤ ማስጨበጫና የንቅናቄ መድረኮች እየተካሄዱ መሆኑን ተናግረዋል።