ቀጥታ፡

ሊድስ ዩናይትድ ቼልሲን ሲያሸንፍ ሊቨርፑል ከሰንደርላንድ አቻ ተለያይተዋል 

አዲስ አበባ፤ ሕዳር 25/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት ሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ትናንት ማምሻውን ተደርገዋል።

ሊድስ ዩናይትድ ቼልሲን 3 ለ 1 በማሸነፍ ወሳኝ ድል አስመዝግቧል።

በኢላንድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጃካ ቢጆል፣ አኦ ታናካ እና ዶምኒክ ካርቨርት ሉዊን ግቦቹን አስቆጥረዋል። 

ፔድሮ ኔቶ ለቼልሲ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል።

የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል ከሰንደርላንድ ጋር በሜዳው አንድ አቻ ተለያይተዋል። 

የሰንደርላንዱ ኖርዲ ሙኪሌ በራሱ ላይ ለሊቨርፑል፣ ኬምስዳይን ታልቢ ለሰንደርላንድ ግቦቹን አስቆጥረዋል።


 

በጥሩ ብቃት ላይ የሚገኘው አስቶንቪላ ከሜዳው ውጪ ብራይተንን 4 ለ 3 አሸንፏል።

ኦሊ ዋትኪንስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አማዱ ኦናና እና ዶንየል ማለን ቀሪዎቹን ጎሎች ለአስቶንቪላ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።

ለብራይተን ጃን ፖል ቫን ሄከ ሁለት ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ የአስቶንቪላው ፖው ቶሬስ በራሱ ላይ አስቆጥሯል።

ውጤቱን ተከትሎ አስቶንቪላ በ27 ነጥብ የሶስተኝነት ደረጃን ከቼልሲ ተረክቧል።

በሌሎች ጨዋታዎች ክሪስታል ፓላስ በርንሌይን፣ ኖቲንግሃም ፎረስት ዎልቭስን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል።

አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ አርሰናል በማይክል ሜሪኖ እና ቡካዮ ሳካ ግቦች ብሬንትፎርድን 2 ለ 0 በማሸነፍ የሊጉን መሪነት አጠናክሯል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም