ቀጥታ፡

የገጠር ትራንስፎርሜሽንን በቅንጅት ማሳለጥ የሚያስችል የ10 ዓመት ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቷል -ግብርና ሚኒስቴር

አዲስ አበባ፤ ህዳር 23/2018(ኢዜአ)፦ የገጠር ትራንስፎርሜሽንን በቅንጅት ማሳለጥ የሚያስችል የ10 ዓመት ፍኖተ ካርታ መዘጋጀቱን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ።

የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት "የገጠር ትራንስፎርሜሽንን በማሳደግ ውጤታማና ባለብዙ ዘርፍ የትብብር ተፅዕኖን ማጎልበት" በሚል ሀሳብ የፓናል ውይይት አካሂዷል።

በፓናል ውይይቱ የተገኙት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለሰ መኮንን (ዶ/ር) የገጠር ሽግግርን ለማፋጠን ግብርናውን ከማዘመን ባሻገር ሌሎች ወሳኝ ሥራዎች መኖራቸውን ገልጸዋል።

ግብርናውን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር በተጀመሩ ተግባራት በኩታ ገጠም እርሻ ገበያ ተኮር ምርቶችን በማምረትና አስፈላጊውን መሰረተ ልማት በማሟላት የአርሶ አደሩን ህይወት የሚቀይሩ ውጤታማ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አንስተዋል።

ከግብርናው ባሻገር የገጠር ሽግግርን ለማሳለጥ የተለያዩ ተቋማት ተቀናጅተው የሚሰሩበት የ10 ዓመት ፍኖተ ካርታ መዘጋጀቱን ተናግረዋል።

ፍኖተ ካርታው ግብርናውን ማዘመን፣ የገጠር መሰረተ ልማት መሟላት፣ የገበያ ትስስርና እሴት መጨመርን ጨምሮ ወሳኝ ጉዳዮች የተካተቱበት ነው ብለዋል።

የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ የትምጌታ አስራት በበኩላቸው የግብርና፣ የገጠር እንዲሁም የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር ጎን ለጎን ተቀናጅተው እንዲፈጸሙ እየተሰራ ነው ብለዋል።

ግብርናን ወደ አዲስ ምዕራፍ ለማሸጋገር እንደ ሀገር ያሉ ጸጋዎችን መለየትና ገበያ ተኮር ትርፍ ምርት ማምረት ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል።

የገጠር ሽግግርን ለማምጣት መሰረት የሚጥሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰው፣ ከእነዚህ መካከል የገጠር ኮሪደር ልማት አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) የግብርና ትራንስፎርሜሽን የተሻገረ ገጠር ለመፍጠር መሰረት ነው ብለዋል።

የግብርና ትራንስፎርሜሽን ትርፍ ምርት ከማምረት ባለፈ፣ ሁሉን አቀፍ መሰረተ ልማት ማሟላትና የነዋሪውን ሕይወት ማሻሻል መሆኑንም ተናግረዋል።

የገጠር ትራንስፎርሜሽንን በተሳለጠ መልኩ ለማሳካት የተዘጋጀው ፍኖተ ካርታ ባለድርሻ አካላት በቅንጅት እንዲሰሩ ያግዛል ብለዋል።

የመንግስት፣ የግል እንዲሁም የምርምር ተቋማት ከአጋር ድርጅቶች ጋር መስራት የተሻገረ ገጠር ለመፍጠር ወሳኝ ሚና እንዳለው ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም