ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአፍሪካን ትርክት የቀየረ የይቻላል ህያው ምልክት ነው-የኢጋድ አባል ሀገራት የሚዲያ ባለሙያዎች - ኢዜአ አማርኛ
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአፍሪካን ትርክት የቀየረ የይቻላል ህያው ምልክት ነው-የኢጋድ አባል ሀገራት የሚዲያ ባለሙያዎች
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 22/2018 (ኢዜአ)፡-ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአፍሪካን ትርክት የቀየረ የይቻላል ህያው ምልክት ነው ሲሉ የ3ኛው የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት አሸናፊና ተሳታፊ የሚዲያ ባለሙያዎች ገለጹ።
በአዲስ አበባ የተካሄደው የ3ኛው የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት አሸናፊና ተሳታፊ የሚዲያ ባለሙያዎች ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን ጎብኝተዋል።
በጉብኝታቸውም ታላቁ የሕዳሴ ግድብ አስድናቂ የምህንድስና ውጤት መሆኑን መመልከታቸውን ጠቅሰው፥ አፍሪካ በራሷ አቅም ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ማሳካት እንደምትችል በማሳየት ትርክት የቀየረ ፕሮጀክት ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት በልዩ ጽናትና በራሳቸው አቅም ግድቡን ማሳካታቸው ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ትምህርት የሰጠና የሚደንቅ ደማቅ አሻራ መሆኑን ገልጸዋል።
ግድቡ የፅናት፣ የራስን መቻል እና የአህጉራዊ ኩራትና የአንድነት ብርሃን መሆኑንም ተናግረዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ሕዝባቸውን በማስተባበር ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ማሳካት እንዳለባቸው ትልቅ ትምህርት መስጠቱንም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ገንዘባቸውን፣ እውቀታቸውን እና ጉልበታቸውን ሳይሰስቱ ለዓመታት በመትጋት እውን ያደረጉት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ አፍሪካ በራሷ አቅም ታላላቅ ፕሮጀክቶችን እንደምታሳካ ህያው ምስክር ነው ብለዋል።
አፍሪካውያን ሜጋ ፕሮጀክቶችን በራሳቸው አቅም ማከናወን አይችሉም የሚለውን የተዛባ ትርክት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሙሉ ለሙሉ መቀልበሱንም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የሕዝቧን የተደመረ አቅም በመጠቀም ብሔራዊ ፕሮጀክቷን እውን አድርጋለች ያሉት የሚዲያ ባለሙያዎቹ ፥ ግድቡ አፍሪካውያን ሲተባበሩ የጋራ ህልማቸውን እውን ማድረግ እንደሚችሉ ማረጋገጫ መሆኑን ገልጸዋል።
የአፍሪካን አቅም፣ ታላቅነትና በልጆቿ ጥረት ግቧን ማሳካት እንደምትችል ህያው ማሳያ መሆኑንም አንስተዋል።
ግድቡ ቀጣናዊ ትስስርን የሚያጠናክርና የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ረገድ ጉልህ አበርክቶ ያለው መሆኑንም የሚዲያ ባለሙያዎቹ ጠቅሰዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው፣ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በሀገር ውስጥና በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያን ዋጋ ከፍለው ያሳኩት አህጉራዊ ፕሮጀክት መሆኑን ተናግረዋል።
ለመላው አፍሪካውያን የኩራት ምንጭ የሆነው ሕዳሴ ግድብ በአህጉሪቱ አዲስ የይቻላል የለውጥ ጉዞን ያቀጣጠለ መሆኑን ገልጸዋል።
የበለጸገችና እና አንድነቷ የጠነከረ አፍሪካን እውን በማድረግ ሂደት ጉልህ ሚና እንደሚኖረውም ጠቁመዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም የበርካታ ሀገራት መሪዎች በተገኙበት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በይፋ መመረቁ ይታወሳል።
#Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ