ድንበር ተሻጋሪው የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር ወዳጅነት - ኢዜአ አማርኛ
ድንበር ተሻጋሪው የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር ወዳጅነት
ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1969 ነው።
ሀገራቱ በተለያዩ ክፍለ አህጉራት የሚገኙ ቢሆንም ርቀት ሳይገድባቸው በዲፕሎሲ እና ኢኮኖሚ መስኮች ያላቸውን ትብብር ቀጥለዋል።
ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር በተለያዩ መስኮች ያላቸውን ግንኙነት ለማስፋት እየሰሩም ይገኛሉ።
ሲንጋፖር በፍጥነት እያደገ የመጣውን የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ፣ ስትራቴጂካዊ ስፍራና ከፍተኛ የህዝብ ብዛት በመጠቀም ትስስሯን የማጎልበት ጠንካራ ፍላጎት አሳይታለች።
እ.አ.አ በ2017 የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን እና የሲንጋፖር የሕብረት ስራ ኢንተርፕራይዝ የተፈራረሙት የጋራ መግባቢያ ስምምነት የዚሁ ማሳያ ነው።
ስምምነቱ ሲንጋፖር በኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማትና የንግድ ስራ ምቹነት ሪፎርሞች ልምዷን የምታካፍልበት ነው። ሎጅስቲክስ፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ግብርና ማቀነባበሪያ፣ ማዕድንና ቱሪዝም ትብብራቸውን ለማጠናከር የጋራ ስምምነት ላይ ከደረሱባቸው መስኮች መከላከል ይጠቀሳሉ።
ኢትዮጵያ ለሲንጋፖር የአፍሪካ የኢንቨስትመንት መግቢያ በር፣ ሲንጋፖር ለኢትዮጵያ የእስያ መግቢያ በር ናቸው ማለት ይቻላል። ሁለቱ ሀገራት በተደጋጋሚ የንግድ እና ኢንቨስትመንትን ጨምሮ አጠቃላይ ትብብራቸውን ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል።
ሌላኛው የሀገራቱ የትብብር መስክ አቪዬሽን ነው። የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር አየር መንገዶች እ.አ.አ በ2012 የአየር አገልግሎት ትብብር ስምምነት መፈራረማቸው ይታወቃል። ስምምነቱ የመንገደኞችና ካርጎ በረራዎችን እንዲሁም የትራንስፖርት ትስስርን ለማጠናከር የሚያስችል ነው።
የአየር አገልግሎት ስምምነቱ በምስራቅ አፍሪካና በደቡብ ምስራቅ እስያ መካከል በጉዞ፣ በካርጎ ንግድ እና ሎጅስቲክስ ያለውን ትብብር ለማጎልበት ያስችላል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እ.አ.አ በ2024 በሲንጋፖር ይፋዊ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወሳል። ጉብኝቱ ሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩበት 55ኛ ዓመት ክብረ በዓል ጋር የተገጣጠመ ነበር።
በጉብኝቱ ወቅት ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር የጋራ መግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱ ሀገራቱ በመደበኛነት የሁለትዮሽ ምክክር እንዲያደርጉ፣ በትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ዘርፍ ያላቸውን ትብብር ማጠናከር የሚያስችል ነው።
ሲንጋፖር በኢትዮጵያ ኤምባሲ እንደምትከፍት ይፋ አድርጋለች። የሲንጋፖር ውሳኔ ከኢትዮጵያ አልፎም ከቀጣናው ጋር በትብብር ለመስራት ያላትን የረጅም ጊዜ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ሆኗል።
የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ዎንግ በቅርቡ በአዲስ አበባ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ከኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጋር በሁለትዮሽ እና በባለብዙ ወገን ትብብራቸው ዙሪያ መክረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ውይይቱ በሁለቱ ሀገሮች መካከል ያለውን ግንኙነት ለጋራ ነጋችን ወሳኝ በሆኑ መስኮች በጋራ ለመሥራት በምናደርገው ጥረት ውስጥ አንድ ጠቃሚ ርምጃ ነው ሲሉም ገልጸውታል።
በተለይም በክሂሎት ልማት እና የካርበን ብድር ትብብር ላይ የተፈረሙት የመግባቢያ ስምምነቶች ጽኑ እና ለነገው ገበያ ዝግጁ የሆኑ ሠራተኞችን ለማፍራት ብሎም በአየር ንብረት ጥበቃ ረገድ ዘላቂ፣ ዝቅተኛ ካርበን የሚያወጣ እድገት ለማረጋገጥ ያለንን የጋራ አቋም ያንጸባርቃል ነው ያሉት።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም በላቀ ተግባራዊ ትብብር ንግድ እና ኢንቨስትመንትን በማስፋፋት፣ ዘመናዊ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስን በማልማት፣ በዲጂታል መሠረተ ልማት፣ በገንዘብ ልውውጥ ቴክኖሎጂ፣ ሳይበር ደኅንነትና ሰው ሰራሽ አስተውሎት ያለንን ትብብር ለመጠቀም እጅግ ሰፊ አቅም አለ ነው ያሉት።
ሁለቱም መሪዎች በጉብኝቱ የኢኮኖሚ ትብብርን ለማላቅ፣ ተቋማዊ መስተጋብርን ለማጠናክር ብሎም የወል ቅድሚያዎቻቸውን ከፍ አድርጎ ለመከወን መንገዶችን እንደተመለከቱበትም ተናግረዋል።
ሲንጋፖር በኢትዮጵያ ኤምባሲ ለመክፈት መወሰኗ ከኢትዮጵያ ባለፈ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ትስስር ማጎልበት የሚያስችላትን ማዕቀፍ እንደሚፈጥር የገለጹት ደግሞ የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ዎንግ ናቸው።
ከዚህ በፊት የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር ኢትዮጵያን የጎበኙት እ.አ.አ በ1964 እንደነበር አስታውሰው የሁለቱን ሀገራት ትብብር ማጠናከር እና ለሲንጋፖር አዳዲስ የንግድ በሮች መክፈት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውን አመልክተዋል።
አስተዳደር፣ ትምህርት እና ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ሀገራቱ ግንኙነታቸውን ለማጠናከር ከሚፈልጉባቸው መስኮች መካከል እንደሚጠቀሱ አንስተው የሀገራቱ መሪዎቹ በተገኙበት ከቁልፍ የጋራ ፍላጎቶቻችን ጋር የሚጣጣሙ የክህሎቶች ልማትና የካርቦን ገበያ የጋራ መግባቢያ ስምምነቶችን ተፈራረመናል ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሲንጋፖር በአዲስ አበባ ኤምባሲ ለመክፈት መወሰኗን በደስታ እንደተቀበሉት ተናግረዋል። የኤምባሲው መከፈት ሲንጋፖር ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ብቻ ሳይሆን ከአፍሪካ ህብረት እና ከመላው አፍሪካ ጋር ቁልፍ ትስስር መፍጠሪያ ሆኖ እንደሚያገለግልም አመልክተዋል።
ሲንጋፖር እና ኢትዮጵያ የየቀጣናቸው መግቢያ በር ናቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገራቱ ያላቸውን አጋርነት የበለጠ በማጠናከር ዜጎችን በዘላቂነት ተጠቃሚ የሚያደርግ ድልድል በደቡብ ምስራቅ እስያ እና አፍሪካ መካከል እየገነቡ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር የቅርብ ጊዜ ውይይቶችና የጉብኝት ልውውጦች ሀገራቱ በጋራ ለመልማትና ለማደግ ያላቸውን ቁርጠኝነት ያሳያል። የሁለቱ ሀገራት ትብብር በአፍሪካ እና በደቡብ ምስራቅ እስያ መካከል እንደ ድልድይ ሆኖ የሚያገለግል ነው።