ቀጥታ፡

የመቻል እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታ ዛሬ ይካሄዳል

አዲስ አበባ፤ ሕዳር 18/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት መቻል እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሚያደርጉት ጨዋታ ይጠናቀቃል።

የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ከረፋዱ አራት ሰዓት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሜዳ ይካሄዳል። 

መቻል በሊጉ ካደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች መካከል አራቱን ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። 

በጨዋታዎቹ 11 ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። መቻል በ13 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። 

የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በበኩሉ እስከ አሁን ያከናወናቸውን አምስት ጨዋታዎች አሸንፏል። 20 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ የተቆጠረበት አንድ ግብ ብቻ ነው። 

ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታዎች እየቀሩት በ15 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል።

ሁለቱ ክለቦች ባለፉት ጥቂት ዓመታት በሊጉ ጠንካራ ፉክክር እያደረጉ ከሚገኙ ክለቦች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም