ቀጥታ፡

የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የክብርና የኢኮኖሚ ነፃነት ጉዳይ ነው

አዲስ አበባ፤ ሕዳር 11/2018(ኢዜአ)፦የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የአህጉሪቷ የክብርና የኢኮኖሚ ነፃነት ጉዳይ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ፡፡

በኢትዮጵያ የሩሲያ ኤምባሲ አዘጋጅነት የአፍሪካ ሀገራትን የምግብ ሉዓላዊነት ማረጋገጥን ዓላማ ያደረገ ዓለም አቀፍ ጉባኤ በአዲስ አበባ ተካሂዷል።


 

በዚሁ ወቅት የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ፤ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የአህጉሪቷ የክብርና የኢኮኖሚ ነፃነት ጉዳይ ነው ብለዋል።

የአህጉሪቷን ዜጎች የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረትም ከተረጂነት በመላቀቅ የማይበገር የግብርና ሥርዓት የመገንባት አካል መሆኑን ገልጸዋል።

በኢትዮጵያም በዘመናዊ የግብርና ሥርዓት ምርታማነትን በማሳደግ ቀጣይነት ያለው የምርት ተወዳዳሪነት ዕድገት እየተመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ በሜካናይዜሽን የእርሻ ሥርዓትን በመደበኛና መስኖ ግብርና ምርታማነት ግልጽ ስትራቴጂክ ዕቅድ ነድፋ እየሰራችበት መሆኗንም አብራርተዋል።

በስንዴ ምርታማነት የተመዘገበው ዕድገትም ከጥገኝነት በመላቀቅ ለውጭ ገበያ ማቅረብ ያስቻለ ተጨባጭ ስኬት ማስመዝገብ እየተቻለ መሆኑንም አስገንዝበዋል።


 

በኢትዮ-ሩሲያ መካከልም በትብብር ላይ የተመሰረተ ረጅም ወዳጅነት ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን አንስተዋል።

በቀጣይም የኢትዮጵያን የግብርና ምርታማነት ሥርዓት በሚያሻሽሉ ዘላቂና ስትራቴጂክ የልማትና ኢንቨስትመንት የትብብር መስኮች በጋራ ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗን አስረድተዋል። 


 

በኢትዮጵያ የሩሲያ አምባሳደር ኢቭጌኒ ተርኪሂን፤ ሩሲያ የአፍሪካን ልማትና ዕድገት በመደገፍ የአህጉሪቷ ጠንካራ አጋር ነች ብለዋል።

በቀጣይም የአፍሪካን የግብርና ሥርዓት ለማዘመን በሚደረገው ጥረት ለአህጉሪቷ የሚደረጉ ድጋፎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።

ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ በወሳኝ ምዕራፍ ላይ ትገኛለች ያሉት አምባሳደሩ፤ ለዚህም ከራሷ አልፎ ለውጭ ገበያ ጭምር ለመትረፍ በቁርጠኝነት እየሰራች መሆኗ የሚደነቅ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም