ቀጥታ፡

የማርበርግ ቫይረስን በአጭር ጊዜ ለመቆጣጠር በቅንጅት እየተሰራ ነው - ሚኒስቴሩ

አዲስ አበባ፤ ህዳር 8/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተከሰተውን የማርበርግ ቫይረስን በአጭር ጊዜ ለመቆጣጠር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የጤና ሚኒስቴር ገለጸ።

በዛሬው ዕለት ወደ ቦታው ተንቀሳቃሽ ላቦራቶሪ መላኩም ተገልጿል።

የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ወቅታዊ የጤና ጉዳዮችን በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጂንካ ከተማ ወረርሽኙ መከሰቱ ከተረጋገጠ ህዳር 3 ጀምሮ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በዚህም እስካሁን የ17 ሰዎች የላቦራቶሪ ናሙና ተወስዶ መመርመሩንና ሶስት ሰዎች በሽታው እንደተገኘባቸውም በክሊኒካል ላቦራቶሪ መረጋገጡን ተናግረዋል።

በቫይረሱ መያዛቸው የተረጋገጡ ሰዎች ህይወት ማለፉንም ጠቅሰዋል።

የጤና ሚኒስቴር ወረርሽኙ ከተለየ በኋላ ንክኪ ያላቸው ሰዎችን ከመለየት ጀምሮ የተለያዩ ስራዎች እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ አሁን ላይ የዚህ ቫይረስ ናሙና የመመርመርና የመለየት አቅም እንዳላት ገልፀው፤ በተለያዩ የጤና ተቋማትም የቅድመ ዝግጅት ስራዎች በቅንጅት እየተሰሩ መሆኑንም ተናግረዋል።

በዚህም በአካባቢው ባሉ የጤና ተቋማት የለይቶ ማቆያና ማከሚያ ማዕከላትን የማቋቋም ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።

በጤና ተቋማት የቁሳቁስ ማሟላት ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቁመው፤ የህብረተሰቡን ግንዛቤ የማሣደግ ስራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ ብለዋል።

በዛሬው ዕለትም ወደ ጂንካ ተንቀሳቃሽ ላቦራቶሪ ጉዞ መጀመሩን ጠቁመው፤ በየወረዳው የተቋቋሙ የድንገተኛ ምላሽ ሰጪ ማዕከላት ስራ እንዲጀምሩ መደረጉን ገልጸዋል።

በንክኪ የሚተላለፍ በሽታ በመሆኑ በተለይ ምልክት ካሳዩ ሰዎች ጋር ንክኪን መቀነስ፣ እጅን በሳሙና መታጠብና ሳኒታይዘር መጠቀም ያስፈልጋል ብለዋል።

ይህን ቫይረስ ለመቆጣጠርም የዝግጅትና ቅንጅት ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቁመው፤ የአገልግሎት ሰጪ ግብረ ሃይልን በማቋቋም ቫይረሱ ወደተከሰተበት አካባቢ መላኩን ገልጸዋል።

በአሁን ወቅት የለይቶ ማቆያ ውስጥ ያለ ሰው አለመኖሩን የገለጹት ሚኒስትሯ፤ በሽታው በተከሰተባቸው አካባቢዎች የለይቶ ማቆያ ቦታዎችን ከማዘጋጀት ጀምሮ የህክምና ቁሳቁስና ግብዓት የማሟላት ስራ መሰራቱን ጠቁመዋል።


 

የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር መሣይ ኃይሉ ቫይረሱ ወደ ተከሰተበት አካባቢ ስለ በሽታው ጥልቅ ትንተና የሚሠሩ ቡድኖችን መላካቸውን ተናግረዋል፡፡

የማርበርግ ቫይረስ እ.አ.አ በ1967 በጀርመን ማርበርግ ከተማ መጀመሪያ መከሰቱን ተከትሎ ስያሜውን ማግኘቱ ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም