ቀጥታ፡

ፎረሙ ከተሞች የቴክኖሎጂ መፍለቂያ መሆናቸው በተግባር የታየበት ነው 

አዲስ አበባ፤ ሕዳር 8/2018 (ኢዜአ)፡-10ኛው የከተሞች ፎረም ኤግዚቢሽን በመደመር መንግሥት ከተሞች የቴክኖሎጂ እውቀት መፍለቂያ መሆናቸው በተግባር የታየበት መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ።

10ኛው የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም "የከተሞች ዕድገት ለኢትዮጵያ ልህቀት” በሚል መሪ ሀሳብ በአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል፡፡

በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ 10ኛውን የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም ኤግዚቢሽን ማስጀመራቸው ይታወሳል።

የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትሯ ጫልቱ ሳኒ ፎረሙን አስመልክቶ የተዘጋጀውን ኤግዚቢሽን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።


 

ሚኒስትሯ ጉብኝታቸውን አስመልክቶ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ በኤግዚቢሽኑ በከተሞች ያለውን ከፍተኛ መነቃቃት በተጨባጭ ማየት መቻላቸውን ገልጸዋል።

አውደ ርዕዩ የዜጎች የስራ ባህል እየተቀየረ መምጣቱ በጉልህ የታየበት መሆኑን ጠቁመው ፤ መንግስት ለከተሞች የሰጠው ትኩረት በተጨባጭ ውጤት እየተረጋገጠ መምጣቱን ተናግረዋል።

ከተሞች ባላቸው አቅም እና ጸጋ እየለሙ መሆናቸውን ያነሱት ሚኒስትሯ ኤግዚቢሽኑ የከተሞች የእርስ በእርስ ግንኙነት እንዲጠናከርና ምርጥ ተሞክሮዎችን እንዲለዋወጡ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ነው የገለፁት።


 

ኤግዚቢሽኑ የበለጠ መተዋወቂያ መድረክ ከመሆኑ ባለፈ ከተሞች የተለያዩ የፈጠራ ውጤቶቻቸውን ያሳዩበት መሆኑን ተናግረዋል።

ኤግዚቢሽኑ በመደመር መንግሥት ከተሞች የቴክኖሎጂ እውቀት መፍለቂያ መሆናቸው በተግባር የታየበት መሆኑን አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም