ቀጥታ፡

መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ለከተሞች አገልግሎት አሰጣጥ መዘመን ትልቅ እገዛን የሚያደርግ ነው 

አዲስ አበባ፤ ህዳር 7/2018(ኢዜአ)፦መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ለከተሞች አገልግሎት አሰጣጥ መዘመን ትልቅ እገዛን የሚያደርግ መሆኑን የኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ሀይሌ (ዶ/ር) ገለጹ።

10ኛው የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም "የከተሞች ዕድገት ለኢትዮጵያ ልህቀት” በሚል መሪ ሀሳብ በአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያ ከተማ መካሄድ ጀምሯል፡፡ 

በሁለተኛው ቀን ውሎም "የኢትዮጵያ የፐብሊክ ሰርቪስ ሪፎርም እና መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት" በሚል የፓናል ውይይት ተካሂዷል።

የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ሀይሌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የመንግስት አገልግሎት እና አስተዳደር ሪፎርም የተነደፈው ለሁሉም ሴክተር ነው። 


 

እንዲሁም ዘመን ተሻጋሪ ተቋማት መገንባትን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ እሳቤው የሰራተኛን የአቅም ክፍተቶችን በመለየት የማብቃት ስራ መሆኑን አንስተዋል።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጭነት የተጀመረው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የዓለምን ምርጥ ተሞክሮዎች በመውሰድ በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ መተግበሩን ጠቁመዋል።

ዓላማውም በከተሞች አገልግሎትን በአንድ ቦታ መስጠት እና የተገልጋዮችን እርካታ ማረጋገጥ መሆኑን ተናግረዋል።

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ለከተሞች አገልግሎት አሰጣጥ መዘመን ትልቅ እገዛን የሚያደርግ መሆኑን ጠቁመዋል።


 

ስርዓቱ አካታች ለሁሉም ዜጋ ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሆኑን ገልጸው፤ የመሶብ ዋና ማእከል በዚህ ዓመት ግንባታው እንደሚጀመር ተናግረዋል።

እስካሁን 21 የመሶብ ማእከላት ወደ ስራ መግባታቸውን ገልጸው፤ በዚህ ዓመት 70 ተጨማሪ ማእከላት ተመርቀው ወደ ስራ እንደሚገቡ አመላክተዋል።

የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እንደ ሀገር የበለጸገች ሀገር የመገንባት ጥረቶች አንዱ አካል መሆኑን በመግለጽ፤ ለአገልግሎቱ የሚያስፈልጉ መሰረተ ልማቶችን ቅድሚያ ሰጥቶ መስራት እንደሚገባም አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም