ለበጋ መስኖ ስንዴ የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ አቅርቦት በስፋት እየተከናወነ ነው-ግብርና ሚኒስቴር - ኢዜአ አማርኛ
ለበጋ መስኖ ስንዴ የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ አቅርቦት በስፋት እየተከናወነ ነው-ግብርና ሚኒስቴር
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 1/2018(ኢዜአ)፡- ለ2018 በጀት ዓመት የበጋ መስኖ ስንዴ ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ አቅርቦት በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ።
የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የአርሶ አደሩን የስራ ባህል በመቀየር በዓመት ከሁለት ጊዜ በላይ እየተመረተ ይገኛል።
ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ለስንዴ ምርት ልዩ ትኩረት በመስጠት የበጋ መስኖን ጨምሮ የስንዴ ምርትና ምርታማነት በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል።
በዚህም የስንዴ ልማት ከሀገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለውጭ ገበያ በማቅረብ የተሳካ ውጤት እየተገኘበት ነው።
በግብርና ሚኒስቴር የሰብል ልማት መሪ ስራ አስፈጻሚ ኢሳያስ ለማ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በ2018 የበጋ መስኖ ስንዴ 4 ነጥብ 29 ሚሊየን ሄክታር መሬት በማረስ 175 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለማምረት እቅድ ተይዞ እየተሰራ ነው።
በዚህ ዓመት የበጋ መስኖ ስንዴ ባለፈው ዓመት ከነበረው የ3 ነጥብ 5 ሚሊየን ሄክታር ብልጫ እንዳለውም ገልጸዋል።
በዘንድሮው የበጋ መስኖ ስንዴ እስከ አሁን ከ767 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማረስ ከ359 ሺህ ሄከታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን ጠቁመዋል።
በዚህም በሀገር አቀፍ ደረጃ በበጋ መስኖ ስንዴ የተገኘውን ልምድ የበለጠ በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚያስችል መልኩ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
ለዚህም የአፈር ማዳበሪያ፣የምርጥ ዘርና እና የውሃ ፓምፕ አቅርቦት ተደራሽ መደረጉን ገልጸዋል።
ከመኸር ምርት የተረፈ እና ለመስኖ የተዘጋጀ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሮች መከፋፈሉንም ተናግረዋል።
የስንዴ ምርጥ ዘርም በበቂ ሁኔታ ለበጋ መስኖ ስንዴ ተደራሽ መደረጉን ገልጸዋል።
የበጋ መስኖ ስንዴ ከዓመት ወደ ዓመት ትልቅ እመርታ እያስመዘገበ መምጣቱንም ተናግረዋል።
የስንዴ ምርት ከሀገር ውስጥ ፍጆታ አልፎ ወደ ውጭ መላክ መጀመሩን አስታውሰው፤ ስንዴ በምግብ ራስን ከመቻል ጋር እንደ ሀገር የተጀመረው ስኬት ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል።
በዚህ ዓመት የበጋ መስኖ ስንዴ የተያዘው ግብ እንዲሳካ የግብርና ባለሙያዎች ድጋፍና ክትትላቸውን እንዲያጠናክሩም ጥሪ አቅርበዋል።