ቀጥታ፡

የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች ምርቶችን በቅርበትና በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመት አስችለዋል

ወላይታ ሶዶ፤ ጥቅምት 30/2018(ኢዜአ)፦ በወላይታ ሶዶ ከተማ የተቋቋሙ የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች ምርቶችን በቅርበትና በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመት እንዳስቻሏቸው የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ።

መንግስት ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ገበያውን ለማረጋጋት ከሚያከናውናቸው ዘርፈ ብዙ ተግባራት ባለፈ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ የሚያገናኝ የገበያ ስርዓት አመቻችቶ ተግባራዊ ማድረጉ ይታወሳል።

በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች የተቋቋሙ የቅዳሜ እና የእሁድ ገበያዎችም የደላላ ጣልቃ ገብነትን በማስቀረት የዜጎችን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ በኩል ጉልህ ሚና እየተጫወቱ መሆኑ ይታወቃል።

አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪዎች የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች ምርቶችን በቅርበትና በተመጣጣኝ ዋጋ በመግዛት ተጠቃሚ እንዳደረጓቸው ተናግረዋል።

ከነዋሪዎቹ መካከል ወይዘሮ ትንሳኤ ሕዝቄል በከተማዋ የተቋቋሙት የቅዳሜ እና እሁድ ገበዎች የተለያዩ ምርቶችን በቅርበትና በተመጣጣኝ ዋጋ በመግዛት የኑሮ ውድነቱን እያቃለለላቸው መሆኑን ገልጸዋል።

በገበያው የተለያዩ የግብርናና የፋብሪካ ምርቶችን በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኙ መሆናቸውንም አንስተዋል።

በገበያዎቹ አቅምና ፍላጎታችንን ያማከሉ ምርቶችን እያገኘን ነው ያሉት ሌላኛዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ ነፃነት ፈለቀ በበኩላቸው ገበያዎቹ ቅርብ በመሆናቸው ጊዜና ወጪ ቆጥበውልናል ብለዋል።

የግብርናና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን ከአርሶ አደሩ እና ከአቅራቢዎች በቀጥታ መግዛታቸው በደላላ ሲደርስባቸው የነበረው የዋጋ ጭማሪ ከማስቅረት ባለፈ ትኩስ ምርቶችን ለመግዛት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል።

ምርቶችን ከአርሶ አደሮች በመግዛት ለሸማቾች በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የኤኪሽን ውሬና ሸማቾች ማህበር ሰብሳቢ ታምራት ካስትሮ ናቸው።

መንግስት በከተማው የግብይት ማዕከላትን በማስፋፋትና በማዘመን ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያደርገው ጥረት መጠናከር እንዳለበት ተናግረዋል።

የወላይታ ሶዶ ከተማ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት መምሪያ ኃላፊ ከበደ ዳና በከተማው የተቋቋሙ የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቾች እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል።

በዚህም ገበያውን በማረጋጋት ለህዝቡ የተሻለ አማራጭ እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቅሰው፣ በቅርቡም በከተማው በሚገኙ 6 ተጨማሪ ቀበሌዎች ገበያዎችን ለመክፈት ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል።

ገበያዎቹ ከሸማቹ በተጨማሪ በማህበር የተደራጁ ኢንተርፕራይዞችንም ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ጨምረው አመልክተዋል፡፡

የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎቹ ለማህበረሰቡ ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ ክትትል እንደሚደረግ ገልጸው፣ በቀጣይ ገበያዎቹ በየቀኑ አገልግሎት እንዲሰጡና ህብረተሰቡ ይበልጥ ተጠቃሚ እንዲሆን በትኩረት ይሰራል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም