በቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ባለሀብቶች ኢንቨስት እንዲያደርጉ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል - ኢዜአ አማርኛ
በቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ባለሀብቶች ኢንቨስት እንዲያደርጉ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 29/2018 (ኢዜአ)፦በቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን የአገር ውስጥና የውጭ ባለሀብቶች ኢንቨስት እንዲያደርጉ ምቹ ሁኔታ መኖሩን የልዩ ኢኮኖሚ ዞኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ቶለሳ በዳዳ ገለጹ።
በቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ውስጥ ማቲዎስ መባ ኮስሞቲክስ ማኑፋክቸሪንግ የግል ድርጅት የኮስሞቲክስ ፋብሪካ ተመርቋል።
በዚሁ ወቅት የቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቶለሳ በዳዳ እንዳሉት፤ የአገር ውስጥም ሆነ የውጪ ባለሀብቶች አስፈላጊ የሆኑ መሰረተ ልማቶች በተሟሉበት በዞኑ በመድሃኒትና በፋርማሲዩቲካል ዘርፎች በስፋት እንዲሰማሩ ጥሪ አቅርበዋል።
አሁን ላይ በልዩ ኢኮኖሚክ ዞኑ ባለሀብቶች በተለያየ የማምረት ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ገልጸው፤ አሁንም ተጨማሪ ባለሃብቶች በመምጣት በሚፈልጉት ዘርፍ ተሰማርተው እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።
በልዩ የኢኮኖሚ ዞኑ አሁን ላይ በቋሚና በጊዜያዊነት ለ4 ሺህ 700 በላይ ዜጎች የስራ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል።
በልዩ ኢኮኖሚ ዞኑ ከውጪ የሚገቡ የመድሃኒትና የፋርማሲዩቲካል ምርቶችን ለመተካት የተለያዩ ኩባንያዎች መድሃኒት እያመረቱ መሆኑን ተናግረዋል።
ማቲዎስ መባ ኮስሞቲክስ ማኑፋክቸሪንግ የግል ድርጅት ባለቤትና ስራ አስፈጻሚ አቶ ማቲዎስ መባ በበኩላቸው፤ ፋብሪካው በመጀመሪያ ዙር በ100 ሚሊዮን ብር ፕሮጀክቱን ማስጀመሩን ገልጸዋል።
ፋብሪካው የኮስሞቲክስ ምርቶችን በአገር ውስጥ በማምረት ከውጪ የሚገባውን ምርት ለመተካት የበኩሉን አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ገልጸው፤ በሙሉ አቅሙ ወደ ስራ ሲገባ ለ260 ዜጎች ቋሚ የስራ ዕድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል።