ቀጥታ፡

ታሪክን የማስቀጠል ትጋት ማሳያ የሆነው የፋሲል አብያተ መንግሥት እድሳት

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 29/2018 (ኢዜአ)፡- የፋሲል አብያተ መንግሥት እድሳት ታሪክን ጠብቆ ለልጆቻችን የማስቀጠል ትጋት ማሳያ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ አስገነዘቡ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት ሥራ ኃላፊዎች የመገጭ የመስኖ ልማት ፕሮጀክትን የሥራ ሁኔታ መገምገማቸውን እና የታደሠውን የፋሲል ግቢ መመረቃቸው ይታወቃል።

ይህን ተከትሎ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በሰጡት ማብራሪያ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) የፋሲል አብያተ መንግሥትን እንዳዩ መጠገን እንዳለበት መወሰናቸውን አውስተዋል።

ይህ ቁርጠኝነትም አንድም የአካባቢውን ብሎም የዓለም ሀብት የሆነውን ቅርስ መታደግ ማስቻሉን ገልጸዋል።

ለመጠገን በነበረው ሂደትም የውስጥና የውጭ ፈተናዎች አጋጥመው እንደነበር አንስተዋል።

ከውጭ ያጋጠመው ፈተና ‘ይህን ቅርስ አትንኩት፤ ከነካችሁት ይፈርሳል፤ እንዳለ ይቀመጥ’ የሚል ትልቅ ተጽዕኖ እንደነበር ጠቁመው፤ የውጭውን ተጽዕኖ በማየትና ‘ጥገናው በሀገር ውስጥ አይቻልም’ የሚሉ አስተሳሰቦችና አመለካከቶች ደግሞ ከውስጥ መነሳታቸውን ተናግረዋል።

እነዚህን ሁሉ ጫናዎች በመስበር ቅርሱ እንደገና ተወልዶ አሁን ለአገልግሎት መብቃቱን አስገንዝበው፤ ከዚህ አንጻር የፋሲል አብያተ መንግሥት ተጠገነ ከሚባል እንደገና ተወለደ ቢባል በይበልጥ ይገልጸዋል ብለዋል።

ይህም ኢትዮጵያ እንደምትችል ያሳል፤ ሌሎች ቅርሶችን ለመጠገን የሚያስችል ዐቅም በሀገር ውስጥ እንዳለንም ይመሠክራል ነው ሉት።

እድሳቱ በሀገር ውስጥ ተቋራጭ በስኬት መከናወኑን ጠቅሰው፤ በለውጡ መንግሥት ትላልቅ የሀገር ውስጥ ተቋራጮች ዐቅም እያደገ መምጣቱን አመላክተዋል።

የፋሲል አብያተ መንግሥት ኢትዮጵያ ታላቅ እንደነበረች፣ አሁንም እንደሆነችና ወደፊትም እንደምትሆን የሚያሳይ ምልክታችን ነው ሲሉም ገልጸዋል።

በሌላ በኩል ከመገጭ ግድብ ጋር በተያያዘ ከተጀመረ ረዥም ዓመታት መውሰዱን ጠቅሰው፤ የአካባቢውን መሬት ከማልማት ባለፈ ለጎንደር ከተማ የመጠጥ ውኃ እጥረት መፍትሔ እንደሚሆን ይጠበቃል ብለዋል።

በተለያዩ ምክንያቶች በመዘግየቱ የመፍረስ አደጋ ተጋርጦበት እንደነበር ጠቅሰው፤ እንደ አዲስ እየተሠራ ያለ ትልቅ ግድብ መሆኑን ተናግረዋል።

ይህም በሀገር ውስጥ ተቋራጭ በጥሩ ሁኔታ እየተሠራ መሆኑን በመጠቆም፤ በዚህ ዓመት ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ አመላክተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም