የድሬዳዋ መሶብ የአንድ ማእከል እንግልትን በማስቀረት ፈጣንና የተቀላጠፈ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል-ተገልጋዮች - ኢዜአ አማርኛ
የድሬዳዋ መሶብ የአንድ ማእከል እንግልትን በማስቀረት ፈጣንና የተቀላጠፈ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል-ተገልጋዮች
ድሬዳዋ፣ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ)፦በድሬዳዋ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት እንግልትን በማስቀረት ፈጣንና የተቀላጠፈ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው ተገልጋዮች ገለጹ።
የድሬ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር እናትዓለም መለሰ እና የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ከድር ጁሃር እና ሌሎችም አመራሮች በተገኙበት መስከረም 15 ቀን 2018 ዓ.ም በይፋ ስራ መጀመሩ ይታወቃል።
በአገልግሎቱ በመጀመሪያው ምዕራፍ አስር የተለያዩ ተቋማት 28 አገልግሎቶች በቴክኖሎጂ ታግዘው እየተሰጡ ሲሆን በዚህም በርካታ ደንበኞች አገልግሎት በማግኘት ላይ ይገኛሉ።
በአገልግሎት ማእከሉ የኢዜአ ሪፖርተር ተገኝቶ ያነጋገራቸው ተገልጋዮች የመሶቦ አንድ ማእከል አገልግሎት እንግልትን በማስቀረት ፈጣንና የተቀላጠፈ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል ብለዋል።
መሶብ ድሬ የአንድ ማዕከል ውስጥ የተገለገሉት ነዋሪዎች ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በዲጂታል አሰራር በተደራጀው ማዕከል ፈጣንና ፍትሃዊ አገልግሎት ለማግኘት አስችሏቸዋል።
ከተገልጋዮቹ መካከል አቶ አበበ አሰፋ እና ወይዘሮ ብርሃኔ ወልደስላሴ፤ አገልግሎቱ ገንዘብንና ጊዜን የሚቆጥብ እንዲሁም እንግልትን የሚያስቀር በመሆኑ አስደስቶናል ብለዋል።
መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ከምንም በላይ ለተገልጋዮች የላቀ ትርጉም ያለው በመሆኑ በሁሉም አካባቢዎች ቢሰፋ መልካም ነው በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ሌሎች ያነጋገርናቸው ተገልጋዮች አቶ አደም አልይ እና አቶ ፈንዲሼ ታጁ፤ በተለያዩ ተቋማት በተራራቁ አካባቢዎች ይሰጥ የነበረውን አገልግሎት በአንድ ስፍራ ላይ በማግኘታችን በጣም የተደሰትንበት አሰራር ነው ብለዋል።
እንዲህ አይነቱ አሰራር መሰረታዊ ለውጥ የሚታይበት እንግልትን በማስቀረት ፈጣንና የተቀላጠፈ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል በመሆኑ ሊሰፋ ይገባል ብለዋል።
የድሬዳዋ የሲቪል ሰርቪስ እና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ በማዕከሉ የተጨማሪ ተቋማትን አገልግሎት ለማስጀመር ዝግጅት እያደረገ መሆኑም ታውቋል።