ቀጥታ፡

በማዕከላዊ ጎንደር ዞን አርሶ አደሩ የዳግም ሰብል ልማት እያካሄደ ነው

ጎንደር ፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ጎንደር ዞን አርሶአደሩ በቀሪ እርጥበት በ50ሺህ ሄክታር ማሳ ላይ የዳግም ሰብል ልማት እያካሄደ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡

የመምሪያው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ፤  በቀሪ እርጥበት የሚካሄደው የዳግም ሰብል ልማት አርሶ አደሩ ተጨማሪ ምርት በማምረት ተጠቃሚነቱን እንዲያሳድግ እያስቻለ መሆኑን ለኢዜአ ገልጸዋል። 

ይህም አርሶ አደሩ ከመኸርና መስኖ በተጨማሪ በዓመት ሶስት ጊዜ በማልማት የምግብ ሉአላዊነቱን ለማረጋገጥ  የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡

ዞኑም ለዳግም ሰብል ልማት ተስማሚ በሆኑ ደጋና ወይና ደጋ አካባቢዎች የሚገኙ አርሶ አደሮችን በመደገፍ  እንደ ስንዴ፣ ገብስ ፣ሽንብራና ጓያ የመሳሰለ ሰብልን በስፋት እንዲያለሙ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

ቀድሞ  የደረሰውን ሰብል በማንሳት በቀሪ እርጥበት ዳግም  የለማውን  ሰብል አርሶ አደሩ በማረምና ከተባይ በመከላከል ላይ መሆኑን ጠቁመው፤ በዳግም ሰብል ልማቱ ለተሳተፉ አርሶ አደሮች የማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘር በማቅረብ ምርታማነቱን ለማሳደግ እየተሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል።

አጠቃላይ በዳግም ከሚለማው መሬት  ከአንድ ነጥብ አራት ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ አመልክተዋል።

በወገራ ወረዳ የባልደርጌ ቀበሌ አርሶአደር ጸጋው ተሾመ በሰጡት አስተያየት፤ ቀሪ እርጥበትን በመጠቀም በግማሽ ሄክታር መሬታቸው ላይ ገብስ በመዝራት እየተንከባከቡ መሆኑን ተናግረዋል።

የዳግም ሰብል ልማቱ በበጋው ተጨማሪ ምርት በማምረት ኑሮዬን እንዳሻሽልና ትርፍ ምርትን ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ሃብት እንድፈጥር ያስችለኛል ብለዋል።

የዚሁ ወረዳ  አርሶአደር በለጠ ግስሙ፤  በቀሪ እርጥበት በመታገዝ ግማሽ ሄክታር የእርሻ መሬታቸው ስንዴ እያለሙ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ከዚህም  17 ኩንታል ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል፡፡ 

በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በ2017/2018 የምርት ዘመን በመኸሩ ወቅት በተለያየ ሰብል  ከለማው 562 ሺህ ሄክታር የእርሻ ማሳ ከ19 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ ከግብርና መምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡ 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም