የሕዳሴ ግድብ አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን በማረጋገጥ ለዲጂታላይዜሽን መሻሻል ትልቅ አስተዋፅኦ ያበረክታል - ኢዜአ አማርኛ
የሕዳሴ ግድብ አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን በማረጋገጥ ለዲጂታላይዜሽን መሻሻል ትልቅ አስተዋፅኦ ያበረክታል
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 26/2018(ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን በማረጋገጥ የዲጂታል አገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን ለማሻሻል ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳለው ተቋማት ገለፁ።
የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለሁለንተናዊ ማክሮ ኢኮኖሚ እድገትና የፋይናንስ አካታችነትን ለማረጋገጥ አስተዋፅኦ እንዳለውም ገልጸዋል።
የኢትዮ ቴሌኮም ቺፍ ሞባይል መኒ ቢዝነስ ኦፊሰር ብሩክ አድሃና ለኢዜአ እንዳሉት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ከዓድዋ ድል በኋላ የአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌትነታችንን የደገምንበት ፕሮጀክት ነው።
የሕዳሴ ግድቡ አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን በማረጋገጥ ለዲጂታላይዜሽን መፋጠን ካለው ፋይዳ በተጨማሪ ለሁለንተናዊ የማክሮ ኢኮኖሚ እድገት ጉልህ አስተዋፅኦ አለው ብለዋል።
ግድቡ የሀገር ውስጥ የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነትን በማሳደግ ለመሰረተ ልማት መስፋፋትና ለሁለንተናዊ የህብረተሰብ እድገት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል።
ዘላቂ የኃይል አቅርቦት የኔትወርክ ጥራትን ለማረጋገጥና የፋይናንስ አካታችነትን ተደራሽ ለማድረግ ሚና እንዳለው አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት የህዝብ ግንኙነትና ኮሙዩኒኬሽን ስራ አስፈፃሚ ሳፊ ገመዲ በበኩላቸው፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያዊያን በጋራ የፈፀምነው ዳግማዊ ዓድዋ ነው ብለዋል።
አገልግሎቱ በሀገሪቱ ተአማኒና ወቅታዊ መረጃ የሚያቀርብ መሆኑን ጠቁመው፣ የተቋሙ 26 ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤቶች የራሳቸው ሰርቨር ያላቸውና ግዙፍ የኃይል አቅርቦት የሚፈልጉ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ግድቡ ዘላቂ የኃይል አቅርቦትን የሚያረጋግጥ መሆኑን ተከትሎ አገልግሎቱ የተሳለጠ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ዘመናዊ የስታትስቲክስ ስርዓት ለመገንባት ለጀመረው ጥረት አስተዋፅኦ እንዳለው ገልፀዋል።
አገልግሎቱ ግድቡ የሚያመነጨውን ሃይል ለዲጂታል ቴክኖለጂ በመጠቀም የሚሰበስበውን መረጃ ጥራት ለማስጠበቅና መረጃ አሰባሰቡን የተሳለጠ ለማድረግ እንደሚያስችለው ነው ያስረዱት።