ቀጥታ፡

የባህር በር ከዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታው ባሻገር ሀገር በአለም አቀፍ ደረጃ የሚኖራትን ተሰሚነት የሚያሳድግ ነው-ምሁራን

ወላይታ ሶዶ፤ጥቅምት 26/2018 (ኢዜአ)፦የባህር በር የማግኘት ጥያቄው ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዳለው ሁሉ አንድ ሀገር በአለም አቀፍ ደረጃ የሚኖራትን የተሰሚነት ተፅዕኖ በአዎንታዊ መልኩ እንደሚያሳድገው በዘርፉ ጥናት ያደረጉ የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ተናገሩ።

የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት በየትኛውም መመዘኛ ህጋዊና ትክክለኛ ጥያቄ በመሆኑ ተገቢ ምላሽ ሊያገኝ ይገባል ሲሉ ነው ምሁራኑ የገለጹት።

የባህር በር ቀጥተኛ የኢንቨስትመንት ዕድልን ከማስፋቱም ባሻገር የአንድ ሃገር ዳር ድንበር ተከብሮ እንዲኖር የሚኖረው ሚና ቀላል አይደለም።

ኢትዮጵያ በተሸረበባት ሴራና በልዩ ልዩ በደሎች ከባህር በር እንድትርቅ የተደረገበት ሁኔታ እጅግ የሚያስቆጭ ጉዳይ መሆኑን ምሁራን ይገልጻሉ።

ሆኖም አሁን በሃላፊነት ላይ ያለው መንግስት ለዘመናት ቁጭት የነበረውን የባህር በር ባለቤትነት አጀንዳን የህልውና ጉዳይ በማድረግ አለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲገነዘበው እያደረገ ያለበት ሁኔታ ይበል የሚያሰኝ ነው።

ኢዜአ ከወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ጋር ባደረገው ቆይታ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በየትኛውም መመዘኛ ህጋዊና ትክክለኛ ጥያቄ በመሆኑ ተገቢ ምላሽ ሊያገኝ ይገባል ብለዋል።

በዩኒቨርሲቲው የታሪክ እና ቅርስ አስተዳደር ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ አበሻ ሺርኮ (ዶ/ር)፥የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ካሉ ተጨባጭ እውነታዎች አንፃር ህጋዊና በግልጽ የቀረበ ጥያቄ መሆኑን አንስተዋል።

የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄው የህልውና ጉዳይ ሆኖ ህጋዊነትን፣ ታሪክንና መልክዓ ምድርን መሰረት በማድረግ የጋራ ተጠቃሚነትን በማለም የተነሳ በመሆኑ ተገቢ ምላሽ ሊሰጠው ይገባል ብለዋል።

በዩኒቨርሲቲው ስነ-ዜጋ እና ስነ-ምግባር ትምህርት ክፍል የሰላምና ደህንነት ትምህርት መምህርና ተመራማሪ ወንድሙ አዴ፤ ኢትዮጵያ ከ30 ዓመታት በላይ የባህር በር አልባ ሆና መቆየቷ ብዙ ዋጋ ያስከፈላት መሆኑን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ከቀይ ባህር የወጣችበት ምክንያት ምንም አይነት ህጋዊ መሰረት ያልተገኘለትና ምንም አይነት ማስረጃ የሌለው መሆኑም ለሁላችንም ጥያቄ ሆኗል ብለዋል።

የባህር በር የማግኘቱ ጥያቄ በየትኛውም መመዘኛ ህጋዊና በትክክለኛ ጊዜ የቀረበ ትክክለኛ ጥያቄ በመሆኑ ተገቢ የሆነ ምላሽ ሊሰጠው እንደሚገባ አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።

የባህር በር የማግኘት ጥያቄው ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዳለው ሁሉ አንድ ሀገር በአለም አቀፍ ደረጃ የሚኖራትን የተሰሚነት ተፅዕኖ በአዎንታዊ መልኩ እንደሚያሳድገውም በዘርፉ ጥናት ያደረጉት ምሁራኑ ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም