የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ በየትኛውም መመዘኛ ህጋዊና ትክክለኛ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ በየትኛውም መመዘኛ ህጋዊና ትክክለኛ ነው
ወላይታ ሶዶ/ጂንካ፤ ጥቅምት 25/2018(ኢዜአ):- የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በየትኛውም መመዘኛ ህጋዊና ትክክለኛ በመሆኑ ተገቢ ምላሽ ሊያገኝ ይገባል ሲሉ ምሁራን ተናገሩ።
የባህር በር የማግኘት ጥያቄው ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዳለው ሁሉ የአንድን ሀገር በአለም አቀፍ ደረጃ የሚኖራትን የተሰሚነት ተፅዕኖ በአዎንታዊ መልኩ እንደሚያሳድገው በዘርፉ ጥናት ያደረጉ ምሁራን ይገልፃሉ።
የባህር በር ቀጥተኛ የኢንቨስትመንት ዕድልን ከማስፋቱም ባሻገር የአንድን ሃገር ዳር ድንበር ተከብሮ እንዲኖር የሚኖረው ሚና ቀላል አይደለም።
ይህና ሌሎች ጉዳዮች ከግምት ሲገቡ ኢትዮጵያ በተሸረበባት ሴራና በልዩ ልዩ በደሎች ከባህር በር እንድትርቅ የተደረገበት ሁኔታ እጅግ የሚያስቆጭ ጉዳይ ነው።
ሆኖም አሁን በኃላፊነት ላይ ያለው መንግስት የበርካታ አመታት የህዝቡ ቁጭት የነበረውን የባህር በር ባለቤትነት አጀንዳን የህልውና ጉዳይ በማድረግ አለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲገነዘበው እያደረገ ያለበት ሁኔታ ይበል የሚያሰኝ ነው።
በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ዙሪያ ሃሳባቸውን እንዲያንፀባርቁ እንዲሁም የኢትዮጵያን የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄና እያደረገች ባለችው ዲፕሎማሲያዊ ጥረት በተመለከተ ኢዜአ ከወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ጋር ቆይታ አድርጓል።
ምሁራኑ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በየትኛውም መመዘኛ ህጋዊና ትክክለኛ ጥያቄ በመሆኑ ተገቢ ምላሽ ሊያገኝ ይገባል ብለዋል።
በዩኒቨርሲቲው የታሪክ እና ቅርስ አስተዳደር ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ አበሻ ሺርኮ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ካሉ ተጨባጭ እውነታዎች አንፃር ህጋዊና በግልጽ የቀረበ ጥያቄ መሆኑን አንስተዋል።
የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄው የህልውና ጉዳይ ሆኖ ህጋዊነትን፣ ታሪክንና መልክዓ ምድርን መሰረት በማድረግ የጋራ ተጠቃሚነትን በማለም የተነሳ በመሆኑ ተገቢ ምላሽ ሊሰጠው ይገባል ብለዋል።
በዩኒቨርሲቲው የስነ-ዜጋ እና ስነ-ምግባር ትምህርት ክፍል የሰላምና ደህንነት ትምህርት መምህርና ተመራማሪ ወንድሙ አዴ፤ ኢትዮጵያ ከ30 ዓመታት በላይ የባህር በር አልባ ሆና መቆየቷ ብዙ ዋጋ አስከፍሏል ብለዋል።
ኢትዮጵያ ከቀይ ባህር የወጣችበት ምክንያት ምንም አይነት ህጋዊ መሰረት ያልተገኘለትና ምንም አይነት ማስረጃ የሌለው መሆኑም ለሁላችንም ጥያቄ ሆኗል ብለዋል።
የባህር በር የማግኘቱ ጥያቄ በየትኛውም መመዘኛ ህጋዊ ጥያቄ በመሆኑ ተገቢ የሆነ ምላሽ ሊሰጠው እንደሚገባ አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።
በተመሳሳይ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በመልክአ ምድር፣ በህግም ይሁን በታሪክ ተቀባይነት ያለው በመሆኑ ተፈፃሚ ሊሆን ይገባል ሲሉ የህግ ምሁራን ተናግረዋል።
ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተገናኘ በጅንካ ከተማ ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የህግ ባለሙያዎች የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በመልክአ ምድር፣ በህግም ይሁን በታሪክ ተቀባይነት ያለው በመሆኑ ተፈፃሚ ሊሆን ይገባል ብለዋል።
የህግ አማካሪና አቃቤ ህግ የሆኑት አቶ ሙሉአለም ኃይለማርያም፤ ኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በየትኛውም መመዘኛ እውነታን የያዘ በመሆኑ ምላሽ ሊሰጠው የሚገባ መሆኑን አስረድተዋል።
በዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊ እና የባህላዊ መብቶች የቃል ኪዳን ስምምነት ላይ ሁሉም ሀገራት በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ትብብር የማድረግ ግዴታ እንዳለባቸው ተደንግጓል ።
በዚህም መሰረት ኢትዮጵያ የቀይ ባህርን የመጠቀም ታሪካዊ፣ ህጋዊ፣ መልካአ ምድራዊ መብት ያላት መሆኑን አስረድተዋል።
ሌላኛው ዐቃቤ ህግ እና የህግ አማካሪ ቢንያም አያሌው፤ የኢትዮጵያ ታሪክ እንደሚያሳየው የሀገሪቱ ስልጣኔና ሌሎች የመንግስት አደረጃጀቶች በዘመናት መካከል ከባህር በር ተለይተው የማያውቁ መሆኑን አንስተዋል።
ኢትዮጵያ ህጋዊ መሰረት በሌለበት መንገድ የባህር በሯን ያጣችበት መንገድ በህግ አግባብ ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ገልጸው፤ ህጋዊ ስምምነት እስከሌለ ድረስ የባህር በር ባለቤት የመሆን መብቷ የተከበረ ሊሆን ይገባል ብለዋል።