ቀጥታ፡

በሰሜን ሸዋ ዞን 44ሺህ ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ለማልማት ተግባራዊ እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው

ደብረ ብርሃን ፤ ጥቅምት 25/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል  ሰሜን ሸዋ ዞን 44 ሺህ ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ለማልማት ተግባራዊ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ።

መምሪያው የበጋ የመስኖ ልማት ማስጀመሪያ የንቅናቄ መድረክ በአንጎለላና ጠራ ወረዳ አካሂዷል።

የዞኑ ግብርና መምሪያ አቶ ታደሰ ማሙሻ በወቅቱ  እንደገለጹት፤  የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የዞኑን  የምግብ ሉአላዊነት ከማረጋገጥ ባሻገር ለገበያ የሚሆን ለማምረት ትኩረት ተሰጥቷል።

ለዚህም  44 ሺህ ኼክታር መሬት  በበጋው ወራት በመስኖ ስንዴ ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን  አስረድተዋል።

በአርሶ አደሮች ተሳትፎ በመስኖ ከሚለማው መሬት  1 ነጥብ 6 ሚሊየን ኩንታል ስንዴ በማምረት ለኢንዱስትሪ ግብአትና ገበያን ለማረጋጋት   መታቀዱን ተናግረዋል።

ባለፉት የለውጥ ዓመታት  አርሶ አደሩ የዝናብ ወቅትን ሳይጠብቅ  ባሉ የውሃ አማራጮች መስኖን በመጠቀም ስንዴን በዓመት ሁለት ጊዜ  በማምረት የምግብ ዋስትናውን እያረጋገጠ መሆኑን ገልጸዋል። 

ምርታማነትን ይበልጥ ለማሳደግም መንግስት የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በወቅቱ እያሰራጨና የግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ  እያደረጉ መሆኑን  ተናግረዋል።

በዞኑ የሲያ ደብርና ዋዩ ወረዳ ግብርና  ጽሕፈት ቤት ሀላፊ አቶ ጥላሁን እንዳላማው ፤  በወረዳው 850 ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ለማልማት ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል።

በወረዳው ከ1 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ   መሬት  በበጋ መስኖ ስንዴ እንደሚለማ  የተናገሩት ደግሞ የአሳግርት ወረዳ ግብርና ጽሕፈት ቤት ሀላፊ አቶ ወሰኔ አምበርብር ናቸው።  

እቅዱን ለማሳካትም የመሬት ልየታ፣ የውሃ መሳቢያ ሞተር አቅርቦትና ሌሎች ዝግጅቶች ተጠናቀው ተግባራዊ ስራው  ተጠናክሮ መቀጠሉን አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም