የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ክፍያ አማራጭ ለደንበኞቹ ምቹ አገልግሎት እየሰጠ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ክፍያ አማራጭ ለደንበኞቹ ምቹ አገልግሎት እየሰጠ ነው
 
           አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 2ዐ/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሀገር በቀል ቴክኖሎጂዎች ክፍያ አማራጭ ለደንበኞቹ ምቹ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን በኢትዮጵያ አየር መንገድ ሆሊደይ፣ዲጅታል ሽያጭ እና ዓለም አቀፍ የደንበኞች ግንኙነት ማዕከል ምክትል ፕሬዝዳንት ኃይለመለኮት ማሞ ገለጹ።
  
 የኢትዮጵያ አየር መንገድ የኦንላይን የክፍያ አማራጭ ስርዓት አቅራቢ ከሆነው ቻፓ ካምባኒ ጋር በጋራ መስራት የሚያስችለውን የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል።
የመግባቢያ ሰነዱን በኢትዮጵያ አየር መንገድ ሆሊደይ፣ ዲጅታል ሸያጭ እና ዓለም አቀፍ የደንበኞች ግንኙነት ማዕከል ምክትል ፕሬዝዳንት ኃይለመለኮት ማሞ እና የቻፓ ካምፓኒ መስራችና ስራ አስኪያጅ ናኤል ሃይለማሪያም ፈርመዋል።
አቶ ኃይለመለኮት ማሞ በዚሁ ወቅት፤ አየር መንገዱ የደንበኞችን አገልግሎት ለማዘመን በርካታ ስራዎችን እየሰራ እንደሚገኝ አመላክተዋል፡፡
በዚህም በተለይ የአሰራር ስርዓቱን በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግ ያከናወናቸው ተግባራት በርካታ ለውጦችን አስመዝግበዋል ነው ያሉት፡፡
በዛሬው እለት ሀገር በቀል ቴክኖሎጂ ከሆነው ቻፓ ካምፓኒ ጋር የተደረገው ስምምነት የሀገር ውስጥና የውጭ ደንበኞችን የኦንላይን የክፍያ ስርዓት ይበልጥ ምቹ እና ቀልጣፋ የሚያደርግ ነው ብለዋል።
ደንበኞች ሞባይል ባንኪንግን፣ቴሌ ብርንና ሌሎች ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የበረራ ትኬቶቻቸውን በኦንላይን እንዲቆርጡ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል።
ሀገር በቀል ቴክኖሎጂዎች ደህንነቱ የተጠበቀ ክፍያን ለመፈጸም ሁነኛ አማራጭ በመሆናቸው የኢትዮጵያ አየር መንገድ እነዚህን ቴክኖሎጂዎች መጠቀሙን አጠናክሮ ይቀጥል፤ድጋፍም ያደርጋል ነው ያሉት።
የቻፓ ካምፓኒ መስራችና ስራ አስኪያጅ ናኤል ሃይለማሪያም በበኩላቸው፤ ቴክኖሎጂው በኢትዮጵያ ውስጥ ደህንነቱ የተጠበቀ እና ለአጠቃቀም ምቹ የሆነ የኦንላይን ክፍያ የሚሰጥ የፋይናንስ ቴክኖሎጂ ነው ብለዋል፡፡
ቴክኖሎጂው በኢትዮጵያ ውስጥ የኢ-ኮሜርስ ንግድ እንዲስፋፋ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ተናግረዋል፡፡
ዓለም አቀፍ እና ከሀገር ውስጥ ደንበኞች ኦንላይን ክፍያዎችን መፈጸም እንደሚያስችል ጠቁመዋል፡፡