የኢትዮጵያን የእንስሳት ሃብት ምርታማነት ለማዘመን የተተገበሩ ቴክኖሎጂዎች የዜጎችን የምግብ ዋስትና እያረጋገጡ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያን የእንስሳት ሃብት ምርታማነት ለማዘመን የተተገበሩ ቴክኖሎጂዎች የዜጎችን የምግብ ዋስትና እያረጋገጡ ነው
 
           አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 20/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን የእንስሳት ሃብት ምርታማነት ለማዘመን የተተገበሩ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች የዜጎችን የምግብ ዋስትና እያረጋገጡ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ።
ከዛሬ ጥቅምት 20 እስከ 22 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ለሶስት ቀናት የሚቆይ የእንስሳት ሃብት ልማት፣ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን የሚያሳይ አውደ ርዕይና ጉባኤ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።
                
                
  
በአውደ ርዕይና ጉባኤው የተለያዩ ሀገራትን የወከሉ የግብርና ዘርፍ የስራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት የእንስሳት ሃብት ልማትና ተዋፅኦ ምርቶች፣ የዓሳና ንብ ማነብ ስራዎችን ለዕይታ ቀርበዋል።
                
                
  
በዚሁ ወቅት በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና ዓሳ ሃብት ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ አለማየሁ መኮንን (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያን የእንስሳት ሃብት ለማዘመን የተተገበሩ ቴክኖሎጂዎች የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጥ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ ነው።
                
                
  
የሌማት ትሩፋትን ጨምሮ በተለያዩ መርሃ ግብሮች ተግባራዊ የተደረጉ የእንስሳት ሃብት ልማት ስራዎች የዜጎችን ተጠቃሚነት እያሳደጉ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
ለአብነትም ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ከፍተኛ የእንስሳት ሃብት ምርታማነት የማሳደግ የዝርያ ማሻሻል ስራ በዜጎች ህይወት ላይ እመርታዊ ለውጥ ለማስመዝገብ ማስቻሉን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ የኔዘርላንድስ አምባሳደር ክርስቲን ፕረን፤ የኢትዮጵያ የግብርና ምርታማነት መርሃ ግብሮች የሀገሪቷን ዕድገት እየደገፉ ነው ብለዋል።
                
                
  
የኔዘርላንድስ መንግስትም የኢትዮጵያን የእንስሳት ሃብትና የግብርና ምርታማነት ልማት የእሴት ሰንሰለት ለማሻሻል ለሚከናወኑ ጥረቶች የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።
የፕራና ኢቨንትስ ማኔጅንግ ዳይሬክተር ነብዩ ለማ፤ አውደ ርዕዩ የኢትዮጵያን የእንስሳት ሃብት ምርታማነት የሚያሻሽል የቴክኖሎጂ ሽግግር፣ የግብዓት አቅርቦትና የገበያ ትስስርን መፍጠር ያስችላል ብለዋል።
                
                
  
የአውደ ርዕዩ ተሳታፊ የሆኑት ዮዲት ቤተ-ማርያም፤ አውደ-ርዕዩ የወተት ማቀነባበሪያ ማሽነሪ ምርቶቻቸውን ለአርሶ አደሩ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ የገበያ ትስስርን ለመፍጠር ከፍተኛ እገዛ እንደሚኖረው ገልጸዋል።
                
                
  
ሌላኛው የአውደ ርዕዩ ተሳታፊ ማዕረግ ገብረ-እግዚአብሔር፤ አውደ ርዕዩ የማር ምርታቸውን በማስተዋወቅ የገበያ ትስስር የሚፈጥሩበት መድረክ ነው ብለዋል።
                
                
  
ከቻይና መጥተው የእንስሳት መኖ ማቀነባባሪያ ቴክኖሎጂን በአውደ ርዕዩ ያቀረቡት ዴቪን ሊዩ፤ ምርታቸውን ለኢትዮጵያና ተሳታፊ ሀገራት እያስተዋወቁ እንደሚገኙ ገልጸዋል።
                
                
  
አውደ ርዕዩ የዶሮ ምርታማነትን የሚሻሽሉ ቴክኖሎጂዎችን በኢትዮጵያ ገበያ ለማቅረብ ዕድል ፈጥሮልናል ያሉት ደግሞ ከቱርክዬ በመምጣት የዶሮ ቤት በአውደ ርዕዩ ያቀረቡት ፉርከን ኤልማሊ ናቸው።