ቀጥታ፡

ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጥራትና ጊዜ እንዲጠናቀቁ የተጠናከረ ድጋፍና ክትትል ይደረጋል

አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 18/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያን ከበለጸጉ ሀገራት ተርታ ለማሰለፍ መሰረት የሚጥሉ ግዙፍ ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጥራትና የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቁ የተጠናከረ ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርጉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ፡፡

ኢትዮጵያ የሕዳሴ ግድብን አጠናቃ ባስመረቀችበት ማግስት የጉባ ብስራቶች የሆኑ የ30 ቢሊዮን ዶላር ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ይፋ አድርጋለች፡፡

እነዚህ ፕሮጀክቶች የማዳበሪያ ፋብሪካ፣ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ጣቢያ ግንባታ፣ የኒውክሌር ሀይል ማበልጸጊያ፣ የጋዝ ማምረት፣ የነዳጅ ማጣሪያ እና በስድስት ዓመታት ውስጥ ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን በላይ ቤቶች ግንባታ ናቸው፡፡

ፕሮጀክቶቹ ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠርና የውጭ ምንዛሬን በማስቀረት ለሕዝቡ የመልማት ፍላጎት ምላሽ የሚሰጡ መሆናቸው ተገልጿል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን ሁለተኛ መደበኛ ስብሰባ ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ ሀገራዊ ፕሮጀክቶቹ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ በመሰረታዊነት የሚቀይሩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል መብራቱ መለስ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ የማዳበሪያ ፋብሪካን ጨምሮ ትላልቅ ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች የውጭ ምንዛሬን በማስቀረት የኢትዮጵያን ብልጽግና የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡


 

ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክቶቹ የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሽግግር የሚያፋጥኑ ወሳኝ ርምጃዎች መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡

ሌላው የምክር ቤት አባል አለሙ ጎንፋ (ዶ/ር) ፕሮጀክቶቹ ኢትዮጵያ ለረጅም ዘመናት ስሟ በድህነት ሲጠቀስ የነበረበትን የታሪክ ምዕራፍ የሚቋጩ እና በሌላ ገጽታ የሚያስተዋውቁ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡


 

ግንባታቸው የተጀመሩና በሂደት ላይ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያን ካደጉ ሀገራት ተርታ የሚያሰልፉ መሆናቸውን ገልጸው፤ የኢትዮጵያን በጎ ገጽታም ይገነባሉ ብለዋል፡፡

ሌላዋ የምክር ቤት አባል አዲሷ አሰፋ ኢትዮጵያ ከራሷ አልፋ ለአፍሪካ ትሩፋት የሚሆኑ የልማት ፕሮጀክቶችን እውን ማድረጓን ገልጸዋል፡፡


 

ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜና ጥራት ተጠናቅቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ የተጠናከረ ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርጉም አረጋግጠዋል፡፡

የምክር ቤት አባላቱ ምክር ቤቱ በህገ መንግስቱ በተሰጠው ስልጣን መሰረት የፕሮጀክቶችን ገቢራዊነት ይከታተላል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም