ቀጥታ፡

ከአማራ ክልል በያዝነው ዓመት 170 ሺህ ኩንታል ጥራቱን የጠበቀ ቡና ለገበያ ለማቅረብ ታቅዷል

‎ባህርዳር ፤ ጥቅምት 18/2018(ኢዜአ)፦ከአማራ ክልል በያዝነው ዓመት 170 ሺህ ኩንታል ጥራቱን የጠበቀ ቡና ለገበያ ለማቅረብ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።

‎በቢሮው የሆልቲካልቸር ባለሙያ አቶ አወቀ ዘላለም ለኢዜአ እንደገለፁት በክልሉ የቡና ልማትን በማስፋፋትና ምርታማነቱን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ ይገኛል።

‎‎በክልሉ በስነ ምህዳርና በአየር ንብረታቸው ተስማሚ በሆኑ አካባቢዎች በኩታ ገጠም ጭምር ከ34 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የቡና ልማት እየተካሄደ መሆኑን ገልፀዋል።

‎ከዚህ ውስጥም ምርት መስጠት ከጀመረው 25 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ 170 ሺህ ኩንታል ጥራቱን የጠበቀ ቡና በማምረት ለአካባቢና ለማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ የለቀማና ምርት ስብስባ እየተካሄደ መሆኑን ተናግረዋል።


 

‎አሁን ላይ ‎‎ለአምራች አርሶ አደሮች ስለቡና ምርት አሰባሰብ፣ አደራረቅና አዘገጃጀት ግንዛቤ በመፍጠር ጥራቱን የጠበቀ ቡና ለማቅረብ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። 

‎‎በምዕራብ ጎጃም ዞን የጃቢጠህናን ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ውበት ተስፌ  ግማሽ ሄክታር በሚጠጋ መሬታቸው ላይ የተሻሻለ ምርት የሚሰጥ የቡና ዝርያ እያለሙ መሆኑን ተናግረዋል።

‎ጥራቱን የጠበቀ ቡና ለገበያ ለማቅረብ ‎የደረሰውን ምርት እየለቀሙ በአልጋ ላይ በማድረቅ  እያዘጋጁ መሆኑን ተናግረዋል።

‎‎የተሻሻለ የቡና ዝርያ  በሩብ ሄክታር መሬታቸው ላይ በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ በአዊ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን የዳንግላ ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሙላቱ እንግዳ ናቸው።


 

‎‎ዘንድሮ ወቅቱ ለቡና ልማት ተስማሚ በመሆኑ የተሻለ የቡና ምርት በመሰብሰብና በመሸጥ ከሰብል ልማቱ ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።

‎በክልሉ ባለፈው በጀት ዓመት 130 ሺህ ኩንታል ቡና ለገበያ መቅረቡን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም