ቀጥታ፡

በዲጂታል ዘርፉ ላይ የተደረገው ሪፎርም በዘርፉ ከፍተኛ  እድገት እንዲመዘገብ አድርጓል- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) 

አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 18/2018(ኢዜአ)፦በዲጂታል ዘርፉ ላይ የተደረገው ሪፎርም በዘርፉ ከፍተኛ እድገት እንዲመዘገብ ማድረጉን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። 

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን ሁለተኛ መደበኛ ስብሰባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ተካሄዷል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ መስከረም 26 ቀን 2018 ዓ.ም ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ ለሁለቱ ምክር ቤቶች የጋራ ስብሰባ ያደረጉትን የመክፈቻ ንግግር አስመልክቶ ከምክር ቤቱ አባላት በቀረቡ ጥያቄዎች ላይ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።

ኢትዮጵያ የ2025 የዲጂታል ቴክኖሎጂ  አካታች የ2030 ስትራቴጂ በመጀመር በዘርፉ የተሻለ እድገት ለማስመዝገብ እየሰራች  ነው ብለዋል።

በኢትዮጵያ ኮደርስ ስልጠና 2 ነጥብ 4 ሚሊዮን ወጣቶች ስልጠናውን  በነጻ መውሰዳቸውን ገልጸዋል።

ለውጡ በተጀመረበት ወቅት 37 ሚሊዮን  የቴሌኮም ተጠቃሚዎች  እንደነበሩ ገልጸው፤ በአሁኑ ወቅት ቁጥሩ 93 ሚሊዮን ደርሷል ነው ያሉት። 

ይህም ሪፎርም በዘርፉ ትልቅ እድገትና ለውጥ እንዲመዘገብ ማድረጉን አመላካች ነው ብለዋል።

በአሁኑ ወቅት 55 ሚሊዮን የሚደርሱ ዜጎች ዲጂታል ባንኪንግ ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁመው፤  በ2028 ዘርፉ 11 ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ሃብት ያመጣል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልፀዋል። 

ከዚሁ ዘርፍ 1 ሚሊዮን ለሚደርሱ ዜጎች የስራ እድል እንደሚፈጠር የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ከዚህም 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር  ገቢ እንደሚገኝ መተንበዩንም ነው የተናገሩት፡፡

በተለይ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍም ሰፋፊ ለውጥና ብቃት እየተመዘገበ  መሆኑን አብራርተው፤ መሶብ የአንድ ማዕከል  አገልግሎትን ጨምሮ ከሚጠበቀው በላይ ስኬታማ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በዲጂታል ዘርፉ ላይ የተካሔደው ሪፎርም ኢትዮጵያ በራሷ አቅም የዲጂታል ገበያ ላይም ስኬታማ ስራዎች እየሰራች መሆኑን አንስተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም