የኮሪደር ልማቱ መዲናዋን ውብ ከማድረግ ባሻገር የንግድ እንቅስቃሴውን በእጀጉ አነቃቅቷል - ነዋሪዎች - ኢዜአ አማርኛ
የኮሪደር ልማቱ መዲናዋን ውብ ከማድረግ ባሻገር የንግድ እንቅስቃሴውን በእጀጉ አነቃቅቷል - ነዋሪዎች
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 16/2018 (ኢዜአ)፡-የኮሪደር ልማቱ መዲናዋን ውብ ከማድረግና የትራንስፖርት መጨናነቅን ከማስቀረቱ ባሻገር የንግድ እንቅስቃሴውን በእጅጉ ማነቃቃቱን ነዋሪዎች ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከብልጽግና ፓርቲ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት ጋር በመሆን የሳር ቤት - ጀርመን አደባባይ - ጋርመንት እና ፉሪ አካባቢ የኮሪደር ልማት ሥራ ጎብኝተዋል።
በሳር ቤት - ጀርመን አደባባይ - ጋርመንት እና ፉሪ የተካሔደው የኮሪደር ልማት በከተማዋ በሁለተኛው ዙር ከተከናወኑ የኮሪደር ልማት ስራዎች መካከል አንዱ ነው።
የኮሪደር ልማቱ 16 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር ርዝመትና 589 ሄክታር መሬት የሚሸፍን ሲሆን፤ በካዛንቺስና አካባቢው ከተካሔደው የኮሪደር ልማት ቀጥሎ በርዝመቱ ሁለተኛ ደረጃ የሚይዝ ነው።
የኮሪደር ልማቱን አስመልክቶ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት የራይድ ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ አቶ ሀብታሙ ግርማ እንደሚሉት፤ የኮሪደር ልማቱ በአካባቢ የነበረውን ሁኔታ ሙሉ ለሙሉ ቀይሮታል።
በተለይም ልማቱ በተሰራበት መንገድ ላይ የነበረውን ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ ያስቀረ፣ የእግረኛና የብስክሌት መንገድን ከአውራ ጎዳና የለየና የንግድ እንቅስቃሴውን የተሻለ ያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ኮሪደር ልማቱ አካባቢውን ለዓይን ማራኪ ከማድረጉ ባሻገር የእግረኛና የተሽከርካሪ መጨናነቅን ማስቀረቱን የገለጹት ደግሞ አቶ ዳንኤል ኩማ ናቸው።
መንግስት ለልማት በሰጠው ከፍተኛ ትኩረት መሰረተ ልማቶቹ እውን መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በመስራት ለውጥ እንደሚመጣ በተጨባጭ እንድናይ አድርጎናል ብለዋል።
አቶ አለሙ አርጋው በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማቱ በሌሎች አገሮች እያየን የምናደንቃቸውን ውብ ከተሞች በራሳችን አገር እንድናይ አድርጓል ነው የሚሉት፡፡
በልማቱ የተሰሩት የስፖርት ማዘውተሪያዎች፣ መናፈሻዎችና ሌሎች የመዝናኛ ቦታዎች ከተማዋን በእጅጉ እንደቀየሯት ተናግረዋል።
ወጣት እየሩስ ፋንታው በበኩሏ በኮሪደር ልማቱ ዘመናዊ መንገዶች መገንባታቸው በአካባቢው ያለው የትራንስፖርት ምልልስ የተሳለጠ እንዲሆን ማስቻሉን ጠቅሳለች።
በአካባቢው የተካሔደው የኮሪደር ልማት የስራ እድል እንደፈጠረላት የተናገረችው ደግሞ ወጣት ሀገሪቱ ፈቃደ ናት።