ቀጥታ፡

ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዘላቂ የኃይል አቅርቦትን በማረጋገጥ ዲጂታላይዜሽንን ለማፋጠን የሚያስችል ነው

አዲስ አበባ፤ጥቅምት 16/2018 (ኢዜአ)፡-ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዘላቂ የኃይል አቅርቦትን በማረጋገጥ ለዲጂታላይዜሽን መፋጠን አስተዋፅኦው የጎላ መሆኑን ምሁራን ገለፁ። 

ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም የተመረቀው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያ ተጨማሪ አምስት ሺህ ሜጋ ዋት በላይ ኃይል እንድታገኝ አድርጓል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ 100 ቀናት የማክሮ ኢኮኖሚ  አፈጻጸም ግምገማን አስመልክቶ በኮይሻ ግድብ ከሚኒስትሮች ጋር ውይይት አድርገዋል።

በዚህ ወቅትም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሚቀጥሉት ወራት ለኢነርጂ እና መስኖ አገልግሎት የሚውሉ መካከለኛ እና ከፍተኛ ግድቦች እንደሚመረቁ ገልጸዋል።

ኢዜአ ያነጋገራቸው ምሁራን እንደገለፁት፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ተጠናቆ ወደ ሃይል አቅርቦት መግባቱ ዘላቂ የኤሌትሪክ ኃይል አቅርቦትን በማረጋገጥ ለዲጂታላይዜሽን መፋጠን አስተዋፅኦው የጎላ ነው። 

በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የአስተዳደር ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንትና የስትራክቸራል ምህንድስና ምሁር ተመስገን ወንድሙ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የኤሌትሪክ ኃይል አቅርቦት ለዘመናዊ የመሰረተ ልማት ግንባታ ወሳኝ ሚና አለው።

ዘላቂ የኤሊትሪክ ኃይል አቅርቦት ለዲጂታላይዜሽን መፋጠን አስተዋፅኦው የጎላ መሆኑን አንስተው፤ የታላቁ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅም ንፁህና ዘላቂ የኃይል ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። 

ከታላቁ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ባለፈ እንደ ኮይሻ ያሉ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫዎች እየተጠናቀቁ መሆን የዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አስቻይ መሆኑን ጠቁመዋል።


 

በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንትና የኤሌክትሪካል ፓወር ምህንድስና ምሁር ከማል ኢብራሂም (ዶ/ር)፤ የታላቁ ህዳሴ ግድብ መመረቅ የሀገሪቷን የኤሌትሪክ ኃይል አቅርቦት በእጥፍ ያሳደገ መሆኑን ተናግረዋል።

ይህም የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ዘላቂነትን በማረጋገጥ ለዲጂታል ቴክኖሎጂ መስፋፋት አስተዋፅኦ ያለው መሆኑንም ገልፀዋል።

የኤሌትሪክ ኃይል አቅርቦት ተደራሽነት መረጋገጥ ከተሜነትን በማስፋፋት ወደ ከተሞች የሚደረግን ፍልሰት ለመቀነስ የሚያግዝ መሆኑንም አስረድተዋል።

ዩኒቨርሲቲው በሰው ኃይል ልማትና በጥናትና ምርምር ዲጂታላይዜሽንን ለማፋጠን ከተለያዩ ተቋማት ጋር በትብብር እየሰራ መሆኑንም አረጋግጠዋል።

የኢሌትሪክ ሃይል አቅርቦት ለድጂታላይዜሽን መስፋፋት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው ሲሆን፤ ከሃይል አቅርቦት ውጭ የዲጂታል ሥርዓት፣ ኔትወርክ፣ ዘላቂነትና ፈጠራእንደማይኖሩ ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም