የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ዘመኑን የዋጁና የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ ናቸው-አቶ አደም ፋራህ - ኢዜአ አማርኛ
የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ዘመኑን የዋጁና የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ ናቸው-አቶ አደም ፋራህ
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 15/2018(ኢዜአ):-በአዲስ አበባ እየተከናወኑ የሚገኙ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ዘመኑን የዋጁና የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ መሆናቸውን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት ጋር በመሆን የተጠናቀቀውን የሳር ቤት-ጀርመን አደባባይ-ጋርመንት እና ፉሪ አካባቢ የኮሪደር ልማት ሥራ ጎብኝተዋል።
በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ የኮሪደር ልማት ጉብኝቱን አስመልክቶ ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በዚሁ ጊዜ የሳር ቤት-ጀርመን አደባባይ-ጋርመንት እና ፉሪ አካባቢ የኮሪደር ልማት ሥራ እስካሁን በከተማዋ ከተከናወኑት በስፋቱ የላቀ ነው ብለዋል።
ከእያንዳንዱ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ትምህርት እየተወሰደ የተሻለ ሥራ እየተሰራ መሆኑን የጠቀሱት አቶ አደም በመዲናዋ የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች የኢትዮጵያን ገጽታ የቀየሩ ናቸው ብለዋል።
የኮሪደር ልማት ሥራዎቹ ከኢትዮጵያ አልፎ ለአፍሪካና ለዓለም ትምህርት የሰጡ መሆናቸውንም ነው ያብራሩት።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተጀመሩትን የኮሪደር ልማት ሥራዎች በየደረጃው ያለው አመራር ተቀብሎ በቁርጠኝነት መተግበሩ ተጨባጭ ውጤት እንዲመዘገብ ማድረጉንም አንስተዋል።
ህዝቡም እያበረከተ ያለው ጉልህ ተሳትፎና ድጋፍ በኮሪደር ልማት የሚፈለገው ውጤት እንዲመጣ የራሱ ሚና አለው ብለዋል።
የኮሪደር ልማት የከተሞችንና የሀገርን ገጽታ ከመቀየር ባሻገር ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው የጎላ መሆኑን በማንሳት፥ ዜጎች የመስሪያና የመሸጫ ቦታ እንዲያገኙና ፍትሐዊ የሃብት ክፍፍል እንዲፈጠር ማድረጉንም ጠቅሰዋል።
በሌላ በኩል የመዝናኛና የስፖርት ማዘወተሪያ ሥፍራዎችን ለሁሉም ዜጋ ተደራሽ እንዲሆኑ በማስቻል አካታች ልማትንና ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል።