በአማራ ክልል 2 ነጥብ 8 ሚሊዮን ተማሪዎችን የምገባ ፕሮግራም ተጠቃሚ የሚያደርጉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በአማራ ክልል 2 ነጥብ 8 ሚሊዮን ተማሪዎችን የምገባ ፕሮግራም ተጠቃሚ የሚያደርጉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
ባሕርዳር፤ ጥቅምት 14/2018 (ኢዜአ) ፡- በአማራ ክልል በዘንድሮው የትምህርት ዘመን 2 ነጥብ 8 ሚሊዮን ተማሪዎችን የትምህርት ቤት ምገባ ፕሮግራም ተጠቃሚ የሚያደርጉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ።
በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር)፤ የተማሪዎች ምገባ አገልግሎት የሚሰጠው በቅድመና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መሆኑን ገልጸዋል።
ለምገባ ፕሮግራሙ የክልሉ መንግስት በጀት መመደቡንና ሌሎች አካላትም ድጋፍ የሚያደርጉበት አቅጣጫ ወርዶ እየተተገበረ መሆኑን አንስተዋል።
የፕሮግራሙ መተግበር የትምህርት ጥራትን ከማረጋገጥ ባለፈ ተማሪዎች ከትምህርት ቤት ሳይቀሩና ሳያሰልሱ ትምህርታቸውን በአግባቡ እንዲከታተሉ ለማስቻል እንደሚያግዝ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት የምገባ ፕሮግራሙ በደሴ፣ በኮምቦልቻና በባህር ዳር ከተሞች መጀመሩን ጠቅሰው፤ በሌሎች ከተሞች፣ በዞኖችና ወረዳዎችም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
የደቡብ ጎንደር ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ደስታ አስራቴ በበኩላቸው፤ በዞኑ በዘንድሮ የትምህርት ዘመን 200 ሺህ ተማሪዎችን የምገባ ፕሮግራሙ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
በአሁኑ ወቅትም በአራት ወረዳዎች የተማሪዎች የምገባ ተግባር መጀመሩን ጠቅሰው፤ የምገባ ፕሮግራሙ በሌሎችም የዞኑ አካባቢዎች እስከተያዘው ወር መጨረሻ ተግባራዊ እንደሚደረግ ተናግረዋል።
በዞኑ በዘንድሮው የትምህርት ዘመን 152 ሺህ ተማሪዎችን ለመመገብ የልየታ ተግባር መከናወኑንና ወደ ተግባርም እንደሚገባ የገለጹት ደግሞ የሰሜን ጎጃም ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ነጋልኝ ተገኘ ናቸው።
የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ትምህርት መምሪያ ኃላፊ ሙሉዓለም አቤ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በትምህርት ዘመኑ 20 ሺህ ተማሪዎች የምገባ ተጠቃሚ እንደሚሆኑና በአሁኑ ወቅትም ተግባራዊ እንቅሰቃሴ መጀመሩንም ገልጸዋል።