ቀጥታ፡

የጥርስ ህመም ተጋላጭነትን ለመቀነስ ምን ይደረግ?

የጥርስ ህመም መንስዔዎችና መከላከል የሚቻልባቸውን ሁኔታዎች በተመለከተ በየካቲት 12 ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ የአፍና የጥርስ ሐኪም እና መምህርት ዶክተር ካሰች አያሌው ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል።

👉 የጥርስ ህመም መንስዔ ምንድን ነው?

ለጥርስና ተያያዥ ህመም አጋላጭ ምክንያቶች በርካታ መሆናቸውን ያነሱት ዶክተር ካሰች፤ ከእነዚህም መካከል፡-

📌 የጥርስ ባክቴሪያ፤

📌 የተመጣጠነ አመጋገብ አለመኖር (ጣፋጭ ምግቦችን ማዘውተር)፤

📌 በትጋት የአፍ ንጽህናን አለመጠበቅ እንዲሁም

📌 ሲጋራ ማጨስ፣ አልኮል መጠጣት፣ ጫት መቃም እና አደጋዎች ጥቂቶቹ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

በተጨማሪም ጭንቀት፣ የሆርሞን ተጽዕኖ፣ የውስጥ የጤና ሁኔታ መታወክ (ለምሳሌ፡- የልብ፣ የኩላሊት፣ የላይኛው መተንፈሻ አካል እና የስኳር ህመም)፣ በዘር ሐረግ የመተላለፍ ሁኔታ፣ በቂ ፍሎራይድ ያለው የጥርስ ሳሙና አለመጠቀምና የብሩሽ ንጽህና መጓደልን በመንስዔነት ዘርዝረዋል።

👉 የጥርስ ህመም ተጋላጭነትን ለመቀነስ ምን ይደረግ?

📌 የአፍ እና የጥርስ ንጽህናን መጠበቅ (ከቁርስና ከእራት በኋላ በቀን ሁለት ጊዜ ከ3 እስከ 5 ደቂቃ ጥርስን መቦረሽ)፤

📌 አመጋገብን ማስተካከል (ጣፋጭ ምግቦችን አለማዘውተር፤ ለጥርስ ጤና ጠቃሚ ምግቦችን መመገብ)፤

📌 ቢያንስ በ6 ወር አንድ ጊዜ የአፍ ውስጥ ጤና ምርመራ ማድረግ፤

📌 በሽታ የመከላከል ዐቅምን የሚጎዱ ተጓዳኝ የጤና ችግሮች ካሉ አስፈላጊውን የሕክምና ክትትል ማድረግ ለጥርስ ህመም የመጋለጥ ዕድልን እንደሚቀንሱ አስገንዝበዋል።

👉 የጥርስ ህመም ያለባቸው ሰዎች ምን ዓይነት ጥንቃቄ ያድርጉ?

📌 የጥርስ ህመም ያለባቸው ሰዎች ወደ ሕክምና ተቋም በመሄድ ያለውን የህመም ሁኔታ በምርመራ አረጋግጠው የሕክምና ዕርዳታ ማግኘት እንደሚጠበቅባቸው መክረዋል።

📌 እንዲሁም ህመሙ እንዳይባባስ የአመጋገብ ሁኔታን ማስተካከል ብሎም ጨው የተጨመረበት ለብ ያለ ውኃን በመጠቀም ከምግብ በኋላ አፍን መጉመጥመጥ እንደሚመከር ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም