ለዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ የሚያስፈልገውን የሰለጠነ የሰው ኃይል የማፍራት ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል - ኢዜአ አማርኛ
ለዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ የሚያስፈልገውን የሰለጠነ የሰው ኃይል የማፍራት ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል

አዲስ አበባ፤ጥቅምት 7/2018 (ኢዜአ)፡-በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ ለሚፈጠሩ የስራ እድሎች የሚያስፈልገውን የሰለጠነ የሰው ኃይል የማፍራት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የስራና ክህሎት ሚኒስቴር አስታወቀ።
የስራና ክህሎት ሚኒስቴር"የነገው የስራ ዓለም"በሚል መሪ ሃሳብ ቀጣሪ ድርጅቶችን እና ተመራቂ ተማሪዎችን ለማገናኘት ያዘጋጀው አውደ ርዕይ እየተካሄደ ነው።
የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታው ሰለሞን ሶካ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፥ የነገው የስራ ዓለም ከቴክኖሎጂ እድገት ጋር የተጣጣመ እንዲሆን ከወዲሁ ዝግጅት እየተደረገ ነው።
ዘርፉ የሚፈልገውን የሰው ኃይል ለማዘጋጀት ገበያ መር የክህሎት ልማት እና ክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራ ላይ በስፋት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ዜጎች ወደፊት በሚኖሩ የስራ እድሎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ መንግስት የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
በኢትዮጵያ የተማሩ ወጣቶች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ተከትሎ ሰፋፊ የስራ እድሎችን ለመፍጠር ሁለንተናዊ ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑን ገልፀዋል።
የመንግስትና የግሉን ዘርፍ ትብብርና አጋርነትን መሰረት ያደረጉ የስራ ስምሪቶችን በማስፋት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል።
አውደ ርዕይውን በትብብር ያዘጋጀው አፍሪ ወርክ ድርጅት ዋና ስራ አስኪያጅ ስመኝ ታደሰ በበኩላቸው፥ አውደ ርዕዩ በቀጣይ ኢትዮጵያ ውስጥ ለሚኖሩ የስራ እድሎች ቀድሞ ዝግጅት በሚደረግባቸው መስክ ላይ ለመወያየት ያለመ መሆኑን ተናግረዋል።
በተለይም ወጣቱ የሰው ሰራሽ አስተውሎትን መሰረት ካደረጉ ቴክኖሎጂዎች ጋር እንዲተዋወቅ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ለመወያየት የተዘጋጀ መሆኑን ነው የገለጹት።
ቀጣሪ ድርጅቶችን ወክለው የተገኙት እሌኒ አምሀ እና ቤቴል ተስፋዬ በበኩላቸው አውደ ርዕዩ ከተለያዩ ድርጅቶች፣የስራ እድል ከሚፈልጉ ዜጎችንና ባለድርሻ አካላት ጋር በቀጥታ ለመገናኘት ዕድል የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል።
ከስራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ ስራ በመፍጠር ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል ስራ መጀመራቸውን ጠቅሰዋል።