ካናዳ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የኢኮኖሚ ትብብር አጠናክራ ትቀጥላለች- አምባሳደር ኒኮላስ ሲማርድ - ኢዜአ አማርኛ
ካናዳ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የኢኮኖሚ ትብብር አጠናክራ ትቀጥላለች- አምባሳደር ኒኮላስ ሲማርድ

አዲስ አበባ፤ጥቅምት 6/2018 (ኢዜአ)፡-ካናዳ ከኢትዮጵያ ጋር በተለያዩ ዘርፎች ያላትን ኢኮኖሚያዊ ትብብር በማስፋት አጠናክራ እንደምትቀጥል በኢትዮጵያ አዲስ የተሾሙት የካናዳ አምባሳደር ኒኮላስ ሲማርድ ገለጹ።
የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ጥቅምት 4 ቀን 2018 ዓ.ም በብሔራዊ ቤተ መንግስት የተለያዩ ሀገራትን አዳዲስ አምባሳደሮች የሹመት ደብዳቤ ተቀብለዋል።
የሹመት ደብዳቤ ካቀረቡት አምባሳደሮች መካከል የካናዳው አምባሳደር ኒኮላስ ሲማርድ ይገኙበታል።
አምባሳደር ሲማርድ በዚሁ ወቅት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ እና ካናዳ ረጅም ዘመን ያስቆጠረ ጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት አላቸው።
የሁለቱ አገሮች ግንኙነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋና እያደገ መምጣቱን ጠቁመው፤ ካናዳ ለኢትዮጵያ ከዋና ዋናዎቹ የልማት አጋሮች አንዷ መሆኗን ገልጸዋል።
አምባሳደር ሲማርድ እንደገለጹት፤ ካናዳ ከኢትዮጵያ ጋር በኤሮስፔስ፣ ማዕድን፣ ትምህርት እና በሌሎችም መስኮች ትብብሯን አጠናክራ ትቀጥላለች።
በተጨማሪም ኢትዮጵያና ካናዳ በምስራቅ አፍሪካ ቀጣና ሰላም እና መረጋጋትን ለማረጋገጥ ተቀራርበው እየሠሩ መሆናቸውን ገልጸው፤ ይህንንም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
በቀጣይ ሁለቱ አገራት አጋርነታቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አምባሳደሩ ተናግረዋል።