ቀጥታ፡

በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖች በምግብ ዋስትና ፕሮግራም ታቅፈው ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ ነው 

ኮምቦልቻ ፤ ጥቅምት 4/2018(ኢዜአ) ፡-በኮምቦልቻ ከተማ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖች በምግብ ዋስትና  ፕሮግራም  ታቅፈው በተደረገላቸው ድጋፍ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ  መሆኑ ተገለጸ።

በከተማ አስተዳደሩ በምግብ ዋስትናና ሴፍቲኔት ፕሮግራም ተጠቃሚዎች እየለማ ያለ ሰብል ዛሬ ተጎብኝቷል።


 

ከተጠቃሚዎች መካከል ወይዘሮ አበባ ፍቃዱ በሰጡት አስተያየት፤ በፕሮግራሙ ታቅፈው  በተመቻቸላቸው የገቢ ማስገኛ ስራ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል።


 

ይህም አካባቢን  በማስዋብና ንጽህናን ከመጠበቁ በተጓዳኝ የተሰማሩበት የጓሮ አትክልት ልማት  የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ አልፈው ምርታቸውን  ለገበያ በማቅረብ ላይ እንደሆኑ አስረድተዋል።

ልማቱን ከጀመሩበት ካለፈው ዓመት የበጋው ወቅት  ወዲህ ድንች፣ ሽንኩርትና ሌሎችንም  አትክልቶችን በማልማት  በሚያገኙት ገቢ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መሆኑን  ገልጸዋል።

በክረምቱ ወራትም  ስንዴን ማልማታቸውንና ሰብሉ በጥሩ  ቁመና ላይ እንደሚገኝ አንስተዋል።

ሌላው የፕሮግራሙ ተጠቃሚ አቶ ጀማል ሰይድ፤  በአካባቢያቸው ጥቅም ላይ ያልዋለ መሬት ተሰጥቷቸው በማልማት  ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን  በማሳደግ ተጠቃሚ እንደሆኑ  ተናግረዋል።


 

በከተማዋ በፕሮግራሙ የታቀፉ  ከ3 ሺህ 490  በላይ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖች በተለያዩ የልማት ስራዎች ላይ መሰማራታቸውን የገለጹት ደግሞ የኮምቦልቻ ከተማ ምግብ ዋስትናና ሴፍቲኔት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ እታፈራሁ አሰግደው ናቸው።


 

የፕሮግራሙ ተጠቃሚዎች በአካባቢ ጽዳት  በመሳተፍ ከሚያገኙት ወርሃዊ ገቢ በተጨማሪ ብድር በማመቻቸት በግብርና፣ በግንባታና ሌሎች ልማቶች  በመሰማራት ተጨማሪ ጥሪት እንዲያፈሩ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

ከዚህ ውስጥም ከ2 ሺህ በላይ የሚሆኑት በከተማ ግብርና በመሳተፍ በዓመት እስከ ሶስት ጊዜ እያመረቱ  በምግብ ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ ትርፍ  ምርታቸውን  ለገበያ  እያቀረቡ  መሆኑን አስረድተዋል።

የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ወንድወሰን ልሳነወርቅ በበኩላቸው፤  በከተማው በፕሮግራሙ  የታቀፉ ወገኖች ጥቅም ላይ ያልዋለ መሬት አልምተው እንዲጠቀሙ በማመቻቸት ውጤታማ መሆናቸውን አብራርተዋል።


 

በጉብኝቱ ላይ  አመራሮች፣ የፕሮግራሙ  ተጠቃሚዎችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም