ቀጥታ፡

በኢትዮጵያ ቁልፍ የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ላይ የሚቃጡ የሳይበር ጥቃቶችን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም ተገንብቷል

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ቁልፍ የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ላይ የሚቃጡ የሳይበር ጥቃቶችን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም መገንባቱን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ ገለጹ፡፡

የአስተዳደሩ ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ተቀርፆ ተግባራዊ ተደረጓል።

ስትራቴጂው ዲጂታላይዜሽን፣ ዘመናዊ አገልግሎት አሰጣጥ አና ቴክኖሎጂን ማዕከል ያደረገ በመሆኑ በሁሉም መስኮች ገቢራዊ እንዲሆን በትኩረት መሰራቱን ገልጸዋል፡፡

ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ዜጎች በቴክኖሎጂ ላይ ያላቸውን አረዳድ በማሳደግ ለዲጂታል መስፋፋት ዕድል ፈጥሯል ብለዋል፡፡

ይሁን እንጂ ከቴክኖሎጂ መስፋፋት ጋር ተያይዞ የሳይበር ጥቃት ይዘቱንና አይነቱን እየቀያየረ እየተከሰተ መሆኑንም አንስተዋል፡፡

በዚህም የሳይበር ጥቃትን ቀድሞ መከላከል የሚያስችል አቅም መገንባት በሚያስችል የወትሮ ዝግጁነት የአሰራር ሥርዓት የቁጥጥርና ምላሽ መስጫ ማዕከላትን በማቋቋም ሁልጊዜም በተጠንቀቅ እየሰራን ነው ብለዋል፡፡

ማዕከላቱን በቴክኖሎጂና በብቁ የሰው ኃይል በማሟላት የቅድመ መከላከልና ዓለም አቀፍ የቁጥጥር ስርዓት በመዘርጋት ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል፡፡

አስተዳደሩ በጥናት የተደገፈ የህግ ማዕቀፍ በማዘጋጀት፣ ፖሊሲና ስትራቴጂ በመቅረጽ በቴክኖሎጂ የተደገፈ የአሰራር ሥርዓት ዘርግቷል ብለዋል፡፡

ባለፈው ዓመት ዘመኑን የዋጀ አዲስ የሳይበር ደህንነት ፖሊሲ መጽደቁን ገልጸው፤ ፖሊሲው ዲጂታላይዜሽንን ከማስረጽ ባሻገር የሳይበር ጥቃትን ለመከላከል ተደራሽነትን ማስፋት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በታዳጊዎች የሰመር ካምፕ የሳይበር ታለንት ማዕከል የሚሰጠው ትምህርት፣ ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር የሚሰሩ የጥናትና ምርምር ስራዎች የዜጎችን ግንዛቤ በማሳደግ ገንቢ ሚና እየተወጡ እንደሚገኙም ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም