ቀጥታ፡

በአፍሪካ ለወጣቶች ክህሎትና ቴክኖሎጂን በማስታጠቅ የፈጠራ አቅማቸውን ማሳደግ ይገባል

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 3/2018(ኢዜአ)፦ በአፍሪካ ለወጣቶች ክህሎትና ቴክኖሎጂን በማስታጠቅ የፈጠራ አቅማቸውን ለማሳደግ በትብብር መሥራት እንደሚገባ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ገለጸ፡፡

ሁለተኛው የአፍሪካ ክህሎት ሳምንት "የአፍሪካን የኢንዱስትሪ መፃኢ ዘመን ለማጎልበት፤ ክህሎት ለኢኖቬሽን፣ ዕድገትና ለዘላቂነት" በሚል መሪ ሀሳብ በአፍሪካ ሕብረት መካሄድ ጀምሯል።


 

የአፍሪካ ክህሎት ሳምንት ለኢንዱስትሪ ዕድገት ኢኖቬሽንና ክህሎትን ለማጠናከር፤ አካታችና ጥራት ያለው የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠናን ለማሳደግ፣ የግሉ ዘርፍና የመንግስትን ትብብር እና ቀጣናዊ ትስስርን ለማጎልበት እንዲሁም የአረንጓዴ ልማትና ቴክኖሎጂን ለማበረታታት ያስችላል ተብሏል፡፡

የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ(ዶ/ር) በጉባኤው መክፈቻ ወቅት እንዳሉት፤ የክህሎት ሳምንት ለአፍሪካ ወሳኝና ስትራቴጂያዊ ጉዳይ ነው፡፡

አፍሪካ በአስቸጋሪና በብዙ ፈተናዎች ውስጥ መሆኗን ገልጸው፤ የወጣቶች ጉዳይ ከንግግር ባለፈ ፈጣን የተግባር ርምጃ የሚያስፈልገው መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ከአፍሪካ ህዝብ አበዛኛው ከ25 ዓመት በታች መሆኑ ትልቅ አቅም ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ነገር ግን ይሄ ኃይል በክህሎትና በቴክኖሎጂ እንዲዳብርና ለፈጠራ እንዲዘጋጅ ማድረግ ይገባል ነው ያሉት፡፡

በአፍሪካ ክህሎትና ፈጠራን በማሳደግ ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ ሽግግር ለማምጣት ወጣቶችን በቴክኖሎጂ ማስታጠቅ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

የአህጉሪቱን የኢንዱስትሪ ምርታማነት ለማሻሻል፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠር፣ ጥራት ያለው አገልግሎት ለመስጠት የወጣቶችን የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን አቅም ማጠናከር ከዛሬ መጀመር እንዳለበት ገልጸዋል፡፡

ወጣቶች ቴክኖሎጂን የሚጠቀሙ ብቻ ሳይሆኑ የሚፈጥሩና ለገበያ የሚያቀርቡ እንዲሆኑ የክህሎት ልማት ልዩ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል፡፡

በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል የህልውና ጉዳይ መሆኑን አንስተውም፤ የአየር ንብረት ለውጥ ፈተናዎችን ወደ ገበያ ዕድል መቀየር እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

ለዚህ ደግሞ ፈጠራ የታከለበት ታዳሽ ኃይልን ማስፋት፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ መገንባት፣ ቀጣይነት ያለው ግብርናን ማሳደግ፣ እንዲሁም ለወጣቶች ሰፊ የሥራ ዕድል መፍጠር ላይ ሊተኮር ይገባል ነው ያሉት፡፡

የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ስርዓት ፍላጎትን መሰረት ማድረግ እንዳለበት ገልጸው፤ ወጣቶች አፍሪካን የሚገነቡ የፈጠራ ሀሳቦችን ማፍለቅ እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡

ሥራ ፈጣሪዎችን ማበረታታትና በቴክኖሎጂ፣ በፖሊሲ እና በአሰራር መደገፍ እንዲሁም አፍሪካውያን መተባበርና የወጣቶች የሥራና የሙያ ነጻ እንቅስቃሴን መፍቀድ አለባቸው ብለዋል፡፡


 

በአፍሪካ ሕብረት የትምህርት፣ ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ኮሚሽን የትምህርት ክፍል ኃላፊ ሶፊያ አሽፓላ፤ ለአፍሪካ አካታች የኢንዲስትሪ አብዮትና የዲጂታል ሽግግር ዕድገት ቀልጣፋ የትምህርትና ስልጠና ሥርዓት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡

የአፍሪካ ሕብረት የወጣቶችን ተሳትፎና የዲጂታል ዕድገት ለማሳለጥ አሕጉራዊ የዲጂታል ሽግግርና ትምህርትና ስልጠና ስርዓት በመቅረጽ መሰረት መጣሉን ገልጸዋል፡፡

ይሄውም በአፍሪካ እውቀትና ኢኖቬሽን መር ማህበረሰብ ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት የሚያሳይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ዲጂታል ቴክኖሎጂ ለኢንዱስትሪ ኢኮኖሚና ማህበረሰብ ዕድገት ቁልፍ መሳሪያ መሆኑን በማንሳት፤ የአፍሪካ ክህሎት ሳምንት የአጀንዳ 2063 እና ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡


 

የ"ሁሉም አፍሪካ ወጣቶች ማሕበር" አማካሪና "የጋራ እሴት" በጋና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አንድሪውስ አኮቶ አዶ በበኩላቸው፤ መሪዎች የአፍሪካን ዕድገትና ኢኮኖሚያዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ በጋራ አጀንዳዎችና መፍትሔዎች ላይ ብዙ ሲሰሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል፡፡

ለዚህ ደግሞ ወጣቶችን የዕቅዶቻቸው ማዕከልና ግንባር ቀደም አድርገው መስራታቸውን ገልጸው፤ ኢትዮጵያ ለዜጎቿ ክህሎት ልማት የወሰደችው ርምጃ ለሌሎች አፍሪካውያን ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም