ቀጥታ፡

በ90 ቀናት ውስጥ እያደገ የመጣውን የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ የሚመልሱ ተግባራት ተከናውነዋል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 3/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ባለፉት 90 ቀናት ውስጥ እያደገ የመጣውን የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ የሚመልሱ ተግባራት መከናወናቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።

ሦስተኛው የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አምስተኛ ዓመት የስራ ዘመን አንደኛ መደበኛ ጉባኤ ተካሂዷል።

የምክር ቤቱ አባላት በተመረጡባቸው አካባቢዎች ከመራጮቻቸው ጋር ባደረጉት ውይይት የተነሱ ጥያቄዎችንና አስተያያቶችን ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ አቅርበዋል።


 

በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ለከተማዋ ነዋሪዎች ተስፋ የሰጡ መሆናቸውን ጠቅሰው፥ የመዲናዋ የኮሪደር ልማት አዲስ አበባን ልዩና ማራኪ ገጽታ እንዳላበሳት ተናግረዋል።

ህብረተሰቡ አዳጊ የሆኑ ጥያቄዎች እንዳሉት ገልጸው፤ በትራንስፖርት እንዲሁም በውሀ አቅርቦት ላይ ያሉ እጥረቶችን በዘላቂነት ለመፍታት ምን እንደታሰበ የምክር ቤቱ አባላት ጠይቀዋል።

የዋጋ ንረትን እንዲሁም የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ምን ይመስላሉ ሲሉም አንስተዋል።

ከአገልግሎት አሰጣጥ አኳያም የሚስተዋሉ ውስንነቶችን ለማቃለል ከተማ አስተዳደሩ እየወሰዳቸው ያሉ እርምጃዎች እንዲብራሩላቸው ጥያቄ አቅርበዋል።

በስራ ዕድል ፈጠራ እንዲሁም ሴቶች እና ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ስራዎች ትግበራ ላይም እየተከናወኑ ባሉ ስራዎች ዙሪያ ምላሽ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ጥራቱ በየነ በሰጡት ማብራሪያ ባለፉት ዘጠና ቀናት ከ96ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶችና ሴቶች የስራ ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል።

ኢንተርፕራይዞች ለመንግስት የልማት ስራዎችና ለኢንዱስትሪዎች የጥሬ እቃ እንዲያቀርቡ በማድረግ የሁለት ቢሊዮን ብር የገበያ ትስስር መፈጠሩን ጠቁመዋል፡፡

በዓመቱ መጨረሻም ለ350ሺህ ወጣቶች የስራ ዕድል ለመፍጠር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጀማሉ ጀምበር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

በቅርቡ ተመርቆ ወደ ስራ የገባው አዲስ የመሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት የዚህ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፤ አገልግሎቱን በሁሉም ክፍለ ከተሞች ለማስፋት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል፡፡

ሀገራዊና ከተማ አቀፍ የተለያዩ ሃይማኖታዊና ህዝባዊ በዓላት በስኬት ማጠናቀቅ መቻሉን ያነሱት ደግሞ በብልፅግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ ናቸው።

ለዚህም የከተማዋ ነዋሪ፣ የፀጥታ መዋቅሩ እና የፖለቲካ አመራሩ የማይተካ ሚና መጫወታቸውን ተናግረዋል፡፡

የእነዚህ ድምር ውጤትም የከተማዋን ገጽታ በመቀየር ከተማዋ የትኩረት ማዕከል እንድትሆን ማስቻሉን ጠቁመዋል።

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በሰጡት ማጠቃለያ የምክር ቤት አባላት ያነሱት ጥያቄ የከተማዋ ህዝብ ዋና አጀንዳና ቅድሚያ የሚሰጠው ልማት መሆኑን ያሳያል።

ጥያቄዎቹ የበለጠ መልማትን የተመለከቱ፣ በርካታ የስራ ዕድል መፍጠርን፣ ተጨማሪ ውጤቶችን ማስመዝገብና ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡ ስራዎች በዘላቂነት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የሚያስችሉ ናቸው ብለዋል።

ባለፉት 90 ቀናት ከከተማ ጀምሮ እስከ ወረዳ ከባለድርሻ አካላትና ህብረተሰቡ ጋር የሚሰሩ ስራዎች በዕቅድ ተይዘው መከናወናቸውን አስረድተዋል።

የአቅመ ደካማና ለሀገር ባለውለታዎች ቤቶችን መልሶ ግንባታና የኑሮ ውድነት ጫና መቀነስ የሚያስችሉ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውንም ገልጸዋል።

በከተማዋ አገልግሎት ማዘመንና የስራ ዕድል ፈጠራ ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው ተግባራት መካከል መሆናቸውን አንስተዋል።

በ90 ቀናት ለማሳካት የታቀዱ ተግባራትን በሙሉ በስኬታማነት መፈጸም መቻሉን ነው ያስረዱት ከንቲባዋ።

ለአብነትም በክረምት ወራት 2ሺ 500 የመኖሪያ ቤቶችን ለመገንባት ታቅዶ የ3ሺህ 400 ቤቶች ግንባታ እየተከናወነ እንደሚገኝና ከእነዚህ መካከልም ከ2ሺህ 500 በላይ የሚሆኑት ተጠናቀው ለህብረተሰቡ መተላለፋቸውን ገልፀዋል።

የኑሮ ውድነት ጫናን ለመቀነስ በቅዳሜና እሁድ ገበያና በሁሉም አካባቢ እየተስፋፉ በሚገኙ የገበያ ማዕከላት ምርቶችን በስፋት በማቅረብ ነዋሪዎች በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን ነው ያብራሩት።

በከተማዋ በርካታ ሁነቶች በስኬትና በድምቀት የተካሄዱት ህዝቡ ከመንግስትና ባለድርሻ አካላት ጋር ተቀራርቦ መስራት በመቻሉ መሆኑንም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም