ሁለተኛው የአፍሪካ ክህሎቶች ሳምንት ዛሬ በአዲስ አበባ ይጀመራል - ኢዜአ አማርኛ
ሁለተኛው የአፍሪካ ክህሎቶች ሳምንት ዛሬ በአዲስ አበባ ይጀመራል

አዲስ አበባ፤ጥቅምት 3/2018 (ኢዜአ)፦ ሁለተኛው የአፍሪካ ክህሎቶች ሳምንት ዛሬ በአፍሪካ ህብረት ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ መካሄድ ይጀምራል።
“አፍሪካውያንን የአፍሪካ የኢንዱስትሪ ልማት የሚያፋጥኑበትን ክህሎቶች ማስታጠቅ” የሳምንቱ መሪ ሀሳብ ነው።
ሁነቱን ያዘጋጁት የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ነው።
በሁነቱ ላይ የአፍሪካ ህብረት ከፍተኛ አመራሮች እና የአባል ሀገራት ሚኒስትሮች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ የኢንዱስትሪ መሪዎች፣ የልማት ተቋማት አመራሮች፣ መምህራን፣ ኢኖቬተሮች፣ የወጣት ተወካዮች እና የልማት አጋሮች ይሳተፉበታል።
የአህጉሪቷን የክህሎት ምህዳር በመቀየር የኢንዱስትሪ ተወዳዳሪነትን ማሳደግ፣ የስራ እድል ፈጠራን ማሳደግ እና ዘላቂ ልማትን ማረጋገጥ ላይ የጋራ ትብብርን ማጠናከር የሁነቱ አበይት ትኩረት ነው።
የአፍሪካ ክህሎት ክፍተትን መሙላት፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ለክህሎት ልማት መጠቀም እና በአጀንዳ 2063 አማካኝነት ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ እድገትን ማረጋገጥ ላይ ውይይት ይደረጋል።
በሳምንቱ የሚኒስትሮች እና የግሉ ዘርፍ የምክክር መድረኮች፣ የክህሎት አውደ ርዕዮች እና የገበያ ትስስር ሁነቶች እንዲሁም የወጣቶች እና የስራ ፈጣሪዎች ፎረም እንደሚካሄድ ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
ፎረሙ የአፍሪካ ኢኖቬተሮች የስራ ውጤቶች የሚቀርቡበት መሆኑን ገልጿል።
የክህሎቶች ሳምንት ተሳታፊዎቹ ኢንዱስትሪ ፓርኮችን፣ በቴክኒክ እና ሙያ ተቋማት እና በኢኖሼሽን ማዕከላት ውስጥ ኢትዮጵያ እያከናወነቻቸው የሚገኙ የሰው ኃይል ልማት ስራዎች ይጎበኛሉ።
ሳምንቱ ሲጠናቀቅ የአፍሪካ ክህሎት ልማትን አስመልክቶ የጋራ አቋም መገለጫ እና የድርጊት መርሃ ግብር ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
የአፍሪካ ክህሎቶች ሳምንት ለአህጉሪቷ የኢንዱስትሪ እና ክህሎት አጀንዳ ተጨባጭ አሻራ የሚያሳርፍ መሆኑን ህብረቱ ገልጿል።
ሳምንቱ እስከ ጥቅምት 7 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ይቆያል።
የመጀመሪያው የአፍሪካ ክህሎቶች ሳምንት እ.አ.አ ኦክቶበር 2024 በጋና አክራ መካሄዱ የሚታወስ ነው::