በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት በማልማት የኢኮኖሚ ጠቀሜታውን ለማሳደግ እየተሰራ ነው-ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻዉ ጣሰው (ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት በማልማት የኢኮኖሚ ጠቀሜታውን ለማሳደግ እየተሰራ ነው-ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻዉ ጣሰው (ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ጥቅምት 2/2018(ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት በማልማት የኢኮኖሚ ጠቀሜታውን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻዉ ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የ2017 አፈጻጸም እና የ2018 የበጋ ወቅት የተቀናጀ የግብርና ልማት ሥራዎች ንቅናቄ መድረክ በዱራሜ ከተማ ተካሂዷል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻዉ ጣሰው (ዶ/ር) በንቅናቄ መድረኩ ማጠቃለያ በሰጡት የስራ መመሪያ እንደገለጹት፤ በክልሉ ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ኢኮኖሚ ጠቀሜታ ለማሳደግ እየተሰራ ነው።
የክልሉ መንግስት የግብርናና የኢንቨስትመንት አማራጮችን በማሳፋትም ለስራ እድል ፈጠራ ለማዋል ትኩረት መስጠቱን አስረድተዋል።
ለተግባራዊነቱም ጥራት ያለው እቅድ ማዘጋጀትና በቅንጅት መተግበር ተገቢ መሆኑን ተናግረዋል።
በተለይም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የግብርናውን ኢኮኖሚ አቅም እውን ማድረግ እንደሚገባ ጠቁመዋል።
ለዚህም ግብዓቶችን ተደራሽ ማድረግ፣የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን መጠቀምና የጥናትና ምርምር ስራዎችን ወደ ተግባር መቀየር ተገቢ ስለመሆኑም አብራርተዋል።
አርሶ አደሩን በቅርበት የሚደግፉ ባለሙያዎች ሙሉ አቅማቸውን ተጠቅመው እንዲሰሩ ማድረግ ላይ ማተኮር ይገባል ሲሉም ጠቁመዋል።
በክልሉ የኤክስፖርት ምርት ማሳደግና፣ተኪ ምርቶችን በማምረት በገጠር እና በከተማ ለወጣቶች የስራ እድል መፍጠር ላይ ማተኮር እንደሚገባም ርዕሰ መስተዳድሩ አሳስበዋል።
የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለሰ መኮንን (ዶ/ር ) በበኩላቸው፤ የሀገርን ሀብት ታሳቢ ያደረገ የግብርና የኢኮኖሚ ሪፎርም ተግባራዊ እየተደረገ ነው ብለዋል።
በግብርናው ዘርፍ በሀገር እና በቤተሰብ የምግብ እና የስርዓተ ምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥም የፖሊሲው ዓላማ መሆኑን ጠቁመዋል።
የኤክስፖርት ምርትን በአይነት፣ በመጠንና በጥራት በማምረት ላይ እንዲሁም ተኪምርቶችን ማስፋትም የትኩረቱ አካል መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው አስገንዝበዋል።
የግብርናውን ዘርፍ ለስራ እድል ፈጠራና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚተገበሩ ኢኒሼቲቮች ማሳካት እንደሚገባም ጠቁመዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና ክልሉ ግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር እንደገለጹት ለግብርናው ዘርፍ መዘመን በዋነኛነት የአርሶ አደር ማሰልጠኛ ተቋማት ድርሻ ከፍተኛ ነው።
ተቋማቱ የምርምር ስራዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ ድህነትን ለማሸነፍ በሚደረገው ጥረት ድርሻቸውን እንዲያጠናክሩም አሳስበዋል።
በመድረኩ በ2017 በጀት ዓመት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ተቋማትና ግለሰቦች የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።