ቀጥታ፡

የክላስተር ግብርና ምርትና ምርታማነትን በ30 በመቶ እንደሚጨምር ተረጋግጧል

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 1/2018 (ኢዜአ)፡-የክላስተር ግብርና ምርትና ምርታማነትን በ30 በመቶ እንደሚጨምር በተጨባጭ መረጋገጡን የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ።

በግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ የተመራ የፌደራልና የክልል አመራሮች ቡድን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በቀቤና ልዩ ወረዳ እና በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ በክላስተር የለሙ የተለያዩ የሰብል ምርቶችን ጎብኝቷል።


 

የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የጀመረቻቸው ስራዎች ውጤት እያስገኙ ነው ብለዋል።

በምርቱ ዘመኑ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ20 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መሸፈኑን ጠቁመው፥ ከ12 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት በክላስተር የለማ መሆኑን ጠቅሰዋል። 

የክላስተር ግብርና ምርትና ምርታማነትን በ30 በመቶ እንደሚጨምር ተረጋግጧል ያሉት አቶ አዲሱ፥ ለዚህም ምክንያቱ የክላስተር እርሻ የሜካናይዜሸን አቅምን፣ የግብዓት ተደራሽነትና አጠቃቀምን ለማሳደግ ምቹ በመሆኑ ነው ብለዋል። 

በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ ውጤታማ ተግባራት የኢትዮጵያን ማንሰራራት ዕውን የሚያደርጉ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።

በግብርናው ዘርፍ የውጭ ንግድ ምርቶችን በጥራትና በብዛት የማምረት እንዲሁም ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመተካት የተጀመሩ ስራዎች ውጤት እያስገኙ ነው ብለዋል።

የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን ጠቀመው ከስራ ዕድል ፈጠራ አኳያም ለበርካቶች ዕድል መክፈቱን ጠቁመዋል።

‎በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና ቢሮ ኃላፊ ኡስማን ሱሩር በበኩላቸው የክልሉ መንግስት ጸጋዎችን በመለየት ወደ ልማት እንዲቀየሩ በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን አብራርተዋል።


 

‎የግብርናውን ዘርፍ እመርታ ለማረጋገጥም የተለያዩ የግብርና ኢንሼቲቮች ተቀርጸው ተግባራዊ እየተደረጉ ስለመሆናቸው ጠቅሰዋል።

በክልሉ ምርታማነትን ወደ ከፍተኛ ደረጃ ለማሳደግ እየተሰራ ይገኛልም ብለዋል።

በጉራጌ ዞን የአበሽጌ ወረዳ አርሶ አደር ሙላቱ ወጉ እና ዚያድ በድሩ ዘንድሮ ካለሙት የበቆሎ ምርት ከፍተኛ ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል።


 

በመንግሥት በኩል የተለያዩ ግብዓቶች በወቅቱ መቅረባቸው ምርታማነታቸው እንዲያድግ ማድረጉንም ተናግረዋል።


 

ዘንድሮ እያለሙት ካለው በቆሎ በሄክታር ከ90 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም