በደሴ ከተማ የቱሪስት መዳረሻ ሥፍራዎችን በማልማት ለቱሪስቶች ምቹ የማድረግ ተግባር በስፋት እየተከናወነ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በደሴ ከተማ የቱሪስት መዳረሻ ሥፍራዎችን በማልማት ለቱሪስቶች ምቹ የማድረግ ተግባር በስፋት እየተከናወነ ነው
ደሴ ፤ ጥቅምት 1/2018 (ኢዜአ)፡-በደሴ ከተማ የቱሪስት መዳረሻ ሥፍራዎችን በማልማት ለቱሪስቶች ምቹ የማድረግ ተግባር በስፋት እየተከናወነ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ።
በደሴ ከተማ "ቱሪዝም ለዘላቂ ልማት" በሚል መሪ ሀሳብ የዓለም የቱሪዝም ቀን ለ33ኛ ጊዜ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል።
የመምሪያው ኃላፊ ወይዘሮ ትዕግስት አበበ በዝግጅቱ ላይ እንደገለፁት፣ በከተማው የቱሪስት መዳረሻ ሥፍራዎችን በማልማት ለቱሪስቶች ምቹ የማድረግ ተግባር በስፋት እየተከናወነ ነው።
በዚህም የደሴ ሙዚዬምን በማደስ፣ የአይጠየፍ አዳራሽ እና የመርሆ ቤተ መንግስታትን ለጎብኚዎች ምቹ በማድረግ ዘርፉ እንዲነቃቃ የማድረግ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል።
ለዚህም የቱሪስቶችና የጎብኝዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱንና የቆይታ ጊዜያቸውን በማራዘም ውጤት እየተገኘ መሆኑን አስረድተዋል።
የወሎን የአብሮነት፣ የመቻቻል፣ የፍቅርና የሰላም ተምሳሌትነት በተግባር በማሳየት ወሎን የማስተዋወቅ ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የደሴ ከተማ አስተዳደር ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰይድ የሱፍ በበኩላቸው በከተማው የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻ ሥፍራዎችን በማልማት የቱሪዝም ዘርፉን ለማነቃቃት እየተሰራ ነው።
አሁን ላይ ባለ 5 ኮከብ እና ዘመናዊ ሆቴሎች፣ የእንግዳ ማረፊያዎችና ሌሎች የአገልግሎት መስጫ ተቋማት እየተገነቡ መሆኑን አስረድተዋል።
በቱሪዝም ቀን አከባበር ስነ ስርዓቱ ላይ አመራሮች፣ የቱሪዝም ባለሙያዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።